153.ኃይሉ ወልደፃዲቅ HAILU WOLDETSADIK
ተወዳጅ ሚድያ እና
ኮሚኒኬሽን፣ በቅርቡ ክምችተ-እውቀት / ኢንሳይክሎፒዲያ / በሚል ርእስ የሚድያ እና የኮሚኒኬሽን ባለሙያዎችን ታሪክ በጠንካራ ሽፋን
መጽሀፍ አሳትሞ ያስመርቃል፡፡ ታሪካቸው በመጽሀፉ ውስጥ ከሚሰነድላቸው አሻራ ካኖሩ የሚድያ ሰዎች መካከል ከ1960ዎቹ የሚመደበው
ጋዜጠኛ ኃይሉ ወልደጻድቅ ነው፡፡ ጋሽ ሀይሉ ገና በ17 አመቱ የጀመረውን የሚድያ ስራ ዛሬ ድረስ በፍቅር እየሰራው ይገኛል፡፡ ግለ-ታሪኩ
እንደሚከተለው ተጠናክሯል፡፡
አቶ ኃይሉ ወልደጻድቅ የተወለዱት በ1947
ዓ.ም ጥቅምት 10 አዲስ አበባ ቁስቋም ማርያም እንጦጦ አካባቢ ሲሆን አባታቸው ወልደፃዲቅ ለጠቦ እናታቸው ሸሁት ጊሚሶ በመባል ይታወቃሉ:: በልጅነታቸው ቄራ፥
ቀጨኔ እና መካኒሳ አካባቢ ኖረዋል::
አቶ ኃይሉ ልጆች እና ትዳር አላቸው አሁን የ67
ዓመት የዕድሜ ባለፀጋ ናቸው።
በመጀመሪያ ቄስ ት/ቤት ገብተው ፊደል ከቆጠሩ በኋላ እስከ
4ኛ ክፍል ድረስ ስብስቴ ነጋሲ በሚባል ት/ቤት ተምረዋል። በመቀጠልም 5ኛ እና 6ኛ ክፍል በመካኒሳ ሚሽን ት/ት ቤት ካጠናቀቁ በኋላ በተስፋ ኮኮብ ት/ቤት የ7ኛ እና የ8ኛ ክፍል ትምህርታቸውን ተከታትለው ሲጨርሱ የነጻ የትምህርት እድል አግኝተው በደሴ በሚገኘው የወ/ሮ ስሂን አዳሪ
ት/ቤት በመግባት በ1964ዓ.ም 12ኛ ክፍል አጠናቀዋል። በወቅቱም በነበራቸው የንባብ ፍቅር፥ በቀለም ትምህርት እና በጉብዝናቸው በጉልህ ይታወቁ ነበር። በትምህርት ቤቱም በእንግሊዝኛ ቋንቋ አስተርጓሚነት እንዲያገለግሉ ዕድል ተፈጥሮላቸዋል ።ገና በለጋ እድሜያቸው በሐይቅ ጢስ አባይ ሊማ በሚባለው የመካነ- እየሱስ ቤተ ከርስቲያን የገበሬዎች ማሰልጠኛ ስፍራ በእንግሊዘኛ ቋንቋ አስተርጓሚነት መስራት ችለው ነበር።
አዲስ አባባ ከተመለሱም በኋላ በ1964ዓ.ም በ17 ዓመታቸው የምስራች ድምፅ መገናኛ ዘዴዎች ሬዲዮ ስቱዲዮ ያወጣውን የቅጥር ማስታወቂያ ፈተና አለፉ። የምስራች ድምፅ በመካነ- እየሱስ ቤተ ክርስቲያን በበላይነት የሚመራ የመገናኛ ዘዴዎች ተቋም ነበር። በወቅቱም በወ/ሮ አለም ሰገድ ህሩይ የጋዜጠኝነት ሙያ አሰልጣኝ አማካኝነት፤ በኬንያ ናይሮቢ ሄደው የጋዜጠኝነት
ስልጠና አግኝተው ነበረ።
በ1965ዓ.ም የምስራች ድምፅ ጠዋትና ማታ በቀን የሁለት ሰዓት በሚተላለፈው የሬዲዮ ፕሮግራም መስራት ጀምረው ነበረ። በባልደረባነት ይንበርበሩ ምትኬ ፣ ገነቱ ይግዛው ፣ አዌይቱ ስሜሶ አብረዋቸው ይሰሩ እንደነበረ ያስታውሳሉ። በቋሚነት ያዘጋጇቸው የነበሩት ፕሮግራሞች በከተማችን ምን ይወራል? እና የግብርና ፕሮግራሞች ነበሩ። በወቅቱም በሀገሪቱ ከነበረው ሬዲዮ ጣቢያ በቀዳሚነትና ፣ በፈጠነ ሁኔታ የምስራች ድምፅ ዘገባዎች በማድረሱ በአድማጭ ዘንድ ተደማጭ እና ተአማኒ ነበር። በ1969 ዓ.ም በ22 ዓመታቸው የብስራተ ወንጌል ሬዲዮ ጣቢያ ተጠባባቂ ኃላፊ ሆነው
ተሹመው ለ6 ወር አገልግለዋል።
በ1969 ዓ.ም መጋቢት ወር ላይ ብስራተ ወንጌል የሬዲዮ ጣቢያ በመንግስት ተወርሶ የአብዮታዊት ኢትዮጵያ ድምጽ የዓለም ዓቀፍ አገልግሎት በመባል ስያሜው ከተቀየረ በኋላም በአማረኛ ፕሮግራም ኃላፊነታቸው ቀጥለዋል። በወቅቱ ሶማሊያ ኢትዮጵያን የወረረችበት ጊዜ ስለነበረ በፕሮፖጋንዳ አርቲክል አዘጋጅ እና በጽሁፍ አቅራቢነት አገልግለዋል። በኋላም ከባልደረባቸው ዳሪዮስ ሞዲ ጋር በመሆን በርካታ አድማጭ የነበረውን በየቀኑ የሚዘጋጅ ወቅታዊ ሁኔታን የሚዳስስ በሳል ትንተና ይሰሩ ነበር ። በዚሁ ምክንያትም በ1974
ዓ.ም ወደ ብሄራዊ አገልግሎት እንዲዘዋወሩ ተደርጎ በየቀኑ የ15
ደቂቃ እርዝማኔና ከፍተኛ ተደማጭነት የነበረው የወቅታዊ ፕሮግራም ዋና አዘጋጅ በመሆን አገልግለዋል። በተጨማሪም በ1975
ዓ.ም ከሙሉጌታ ወልደሚካኤል ጋር የ1
ሰዓት እርዝማኔ የነበረው የቅዳሜ ከሰአት የመዝናኛ ፕሮግራምም ያዘጋጁ ነበር። አብረዋቸውም ታገል ሰይፉ ፣ ደረጄ ሃይሌ እና ሀብቴ ምትኩ በተባባሪነት ይሰሩ ነበር ። በወቅቱ ከመንግስት ባለስልጣናትም ጭምር አድናቆት ተችሯቸው ነበር። አቶ ኃይሉ ለስልጠና ወደ ሀንጋሪ አቅንተው ከ6 ወር ቆይታ በኋላ ሲመለሱ የፕሮግራም ክፍል ዋና ኃላፊ ሆነው ተሾሙ።
በ1983
ዓ.ም ኢህአዲግ የመንግስተ ስልጣኑን ከተቆጣጠረ በኋላ ከስራ ከተባረሩት 153 ከፍተኛ የማስታወቂያ ሰራተኛዎች ውስጥ አንዱ አቶ ኃይሉ ወልደፃዲቅ ሲሆኑ ቤተሰባቸውንም ለመደገፍ ከነ አቶ ሙሉጌታ ወልደሚካኤልና አቶ ውብሽት ወርቃለማው ጋር ማስታወቂያ በማንበብ ገቢ ማግኘት ጀምረው ነበር።
በ1984 ዓ.ም አጥቢያ ኮከብ የህትመትና የማስታወቂያ ስራ ድርጅትን (አክፓክ)
ከ15 ባለሙያዎች ጋር መሰረቱ። ስብስቡን የጀመሩት እና ሃሳቡን ያመነጩት አቶ ሙሉጌታ ሉሌና አቶ ወሌ ጉርሙ ናቸው። በወቅቱም አባል የነበሩት እምሩ ወርቁ ፣ ደስታ ወርቁ ፥ ጎሹ ሞገስ ፣ ኤሊያስ ብሩ ፣ አልማዝ ደጀኔ ከብዙሀኑ በጥቂቱ የሚጠቀሱ አባላት ናቸው። መፅሄት ማዘጋጀት ፣ የቴሌቪዥን እና የሬዲዮ ማስታወቂያዎችን መስራት ፣ መፅሀፍ ማሳተም፣ የትርጉም ስራዎችን መስራት ጀመሩ። የመፅሄቱ ን
ለመጀመሪያ ጊዜ
5000 ቅጂ ጦቢያ በሚል ስያሜ አሳተሙ። ነገር ግን ገበያ ላይ በብዛት መሸጥ አልቻለም ነበር። በወቅቱ አንድ የወያኔ ጋዜጠኛ ስለ ጦቢያ መጽሄት ጦቢያ ማለት ጦሩ ቢዋጋ ያሸንፍ ነበረ በማለት የራሱን ትርጉም ሰጥቶ በማቅረቡ ጦቢያ መጽሄት ብዙ አንባቢያንን ትኩረት ሳበ። የመጽሄቱንም ሁለተኛ ህትመት
60000 ቅጂ በመላው ኢትዮጵያ መሰራጨት ቻለ። በወቅቱም የሽያጭ ሃላፊ የነበሩት አቶ ኃይሉ በ4 ወራት ጊዜ ውስጥ ድርጅቱ
የነበረው የሽያጭ ገቢም 1 ሚሊየን በር ገደማ ደርሶ እንደነበረ ይገልጻሉ ። በተጨማሪም ዶክመንተሪ ፊልሞችን መስራት ጀምረው ከፍተኛ ተቀባይነትን ማግኘት ችለው ነበር። ከእነዚህ ውስጥ ለኢትዮጵያ ቤተሰብ መምሪያ የተዘጋጀው እምቡጥ ፅጌረዳ የሚለው ዶክመንተሪ ፊልም ተጠቃሽ ነው። ጦቢያ መፅሄትም ተነባቢነቱና ተፈላጊነቱ ሳይቀንስ ለ11
አመት ለንባብ በቅቷል። በ1997ዓ.ም በኢህአዲግ መንግስት ጣልቃ ገብነት የማሳተም ሂደቱ ተቋርጦ አክ ፓክ የማስታወቂያ ድርጅትም ተዘጋ።
በ1994 ዓ.ም በኤፍኤም 97.1 በዩኒቲ ድምፅ ፕሮግራም የ20
ደቂቃ ዝግጅት ላይ ዋና አዘጋጅ በመሆን ከ ሳምሶን ማሞ ፣ ኤፍሬም እንዳለ፥ ሙሉጌታ ወልደሚካኤል ፣ መለሰ ገስጥ ፣ዋሲሁን ዋጋው ና ደረጄ ሃይሌ ፣ ጋር በመሆን በጋራ ይሰሩ ነበር ።ፕሮግራሙም ማህበራዊ ህይወትን እና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮችን በስፋት የሚዳስስ ተደማጭነት የነበረው አድማጭን በቀጥታ ስርጭት የሚያሳትፍ የሬዲዮ ዝግጅት ነበር። ፕሮግራሙም በአጠቃላይ አየር ላይ ለ6
ወር ቆይታ የነበረው ሲሆን በወቅቱም ብዙዎችን ያስቆጣ እና ብዙዎችንም ያወያየ ዝግጅት ነበር። ቀጥለውም
በዩኒቲ ዩንቨርስቲ የተለያዩ ስራዎች ከሰሩ በኋላ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ሆነው ለ9 አመት
አገልግለዋል።
በ2004 ዓ.ም በአንድነት ኢንተርናሽናል ት/ቤት እና ኮሌጅ የህዝብ ግንኙነት ባለሞያ በመሆንና የኮሌጁ የማታ ትምህርት ክፍል አስተባባሪ ሆነው ለ10 ዓመታት አገልግለው
በቅርቡ ከስራቸው ለቀዋል።
መዝጊያ
አቶ ኃይሉ በህይወታቸው ውስጥም ህይወትን አቅልሎ ወይም አክብዶ መመልከት አይወዱም፡፡ ለኑሯቸውም ምክንያታዊ ናቸው። እጅግ ሲበዛ ትዕግስተኛም ናቸው። ሀገራቸውን አብዝተው ይወዳሉ ፣ ማንበብ የረጅም ጊዜ የህይወት ልምዳቸው ነው። አቶ ኃይሉ ወልደፃዲቅ የነበረውን በማፍረስ ውስጥ ያለው የሀገራችን ሁኔታ አጥብቀው ይቃወማሉ። የሚመክሩትም ያለፈውን ነገር አፍርሶ ከመጀመር ከተሰራው ተነሰተን የተሻለ ነገር እንደ ሀገር መስራትን አጥብቀው ይመክራሉ።
አስተያየቶች
አስተያየት ይለጥፉ