1.  ታዬ በላቸው መልካ-TAYE BELACHEW MELKA 

 








ተወዳጅ ሚድያ እና ኮሚኒኬሽን የሚድያ ሰዎች ታሪክ ከአንጋፋ እስከ ወጣት በሚል ሀሳብ 130 በላይ የሚድያ ሰዎችን ታሪክ ደረጃውን በጠበቀና ጠንካራ ሽፋን/hard cover/ ኢንሳይክሎፒዲያ ሊያሳትም እንደሆነ ይታወቃል፡፡ እስከዚያ ድረስ ታሪካቸው በዚህ ዊኪፒዲያ እና በተወዳጅ ሚድያ የፌስ ቡክ ገጽ ላይ ከሚነገርላቸው መካከል  ጋዜጠኛ እና የህግ ባለሙያ ታዬ በላቸው መልካ ይነሳል፡፡

 

በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ውስጥ በወር 285 (በሁለት መቶ ሰማንያ አምስት ብር) እየተከፈለው "ከየአቅጣጫው" ዓለም እንዴት ሰነበተች?” ቲቪ መስተዋትየሚባሉ ፕሮግራሞችን ያዘጋጅ ነበር፡፡ በኋላም እያደገ መጥቶ የዜና ዋና አዘጋጅ መሆን ችሏል። ኢህአዴግ እስኪገባ ድረስ በነበረው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን (ዘጠኝ) ኣመታት ቆይታ ከሺህ በላይ ዜናዎችንና ፕሮግራሞችን በአድማጭ ተመልካቹ ልብ ውስጥ እና የቴሌቪዥን አርካይቭ ላይ ማስቀመጥ የቻለ ሰው ነው። የቤተመንግስት ሪፖርተር በመሆንም በፓርላማ የሚካሄዱ ሁነቶችን ወደ ህዝቡ ያደርስም ነበር፡፡ጋዜጠኛ በመሆኑና እውነታውን በመፃፉ ብቻ ከአስር ጊዜ በላይ ለእስር ተዳርጓል። ጋዜጠኛ ታዬ በላቸው መልካ         

 

           ልደት እድገትና ትምህርት

 

ጋዜጠኛ እና የህግ ባለሙያ ታዬ መጋቢት 30 ቀን 1949 . በድሬዳዋ ልዩ ስሙ አዲስ ከተማ በሚባል አካባቢ ተወለደ። እናትና አባቱ በድሬዳዋ ረጅም ዘመናትን ያሳለፉ ሲሆን በተለይ የእናቱ ሙሉ ቤተሰቦች ሀረርን እና ድሬዳዋን የመሠረቱ ሰዎች እንደሆኑ ይነገራል። አባቱ አቶ በላቸው መልካ(በላቸው ቅመሙ) ድሬዳዋ ቀፊራ በሚባለው አካባቢ በእህል ንግድ በኦጋዴን ደግሞ በሸቀጥ ንግድ ላይ ለዘመናት የተሰማሩ ነበሩ። ከሰባት ልጆች መካከል ታዬ የቤቱ 3ኛው ልጅ ነው።

 

ታዬ በላቸው አሸዋ ሚካኤል የቄስ ትምህርትን ተምሮ አንደኛ ክፍልን  በዚያው በድሬዳዋ ልኡል መኮንን ትምህርት ቤት ጀመረ። በኋላም ከአያቱ ጋር ወደ አለማያ(ሀሮማያ) ሄዶም ተምሯል፡፡ 4 እስከ 8 ክፍል የተማረው ደግሞ ጂግጅጋ ነዉ፡፡ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ያጠናቀቀዉ በትውልድ መንደሩ በድሬዳዋ ልኡል መኮንን አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ነበር። በትምህርት ቤት ቆይታው የሚኒ ሚዲያ አባል በመሆን ሰኞ ሰኞ የሳምንቱን ዋና ዋና ዜናዎች ሰንደቅ ዓላማ ሲሰቀል ከስፖርት ጋዜጠኛው ደምሴ ዳምጤ ጋር በመሆን ለተማሪዎች ያቀርቡ ነበር።

 

የሁለተኛ ደረጃ ተማሪ ሳለ ነበር በኋላ ለገነነበት የጋዜጠኝነት ሙያው መሠረትን የጣለው።አቶ መኮንን ሸገኔበወቅቱ የነበሩ የትምህርት ቤቱ ዳይሬክተር በትምህርት ቤት ውስጥ ካቋቋሟቸው በርካታ ክበቦች መካከል ታዬም የጂኦግራፊ ክበብ አባል በመሆን የተለያዩ ጉዞዎች በሚደረጉበት ወቅት ፎቶግራፍ አንሺ እና ታሪክ ዘጋቢ እንዲሆን ተመረጠ፡፡ ታዬም በከፍተኛ የደስታ ስሜት መስራት ጀመረ፡፡ ከጓደኞቹ ጋር በመሆን በወቅቱ በድሬዳዋ ከተማ የሚኖሩ ባለሀብቶችን በማስተባበር እርዳታ በማሰባሰብ የመጀመሪያውን በእርዳታ የተገኘ ገንዘብ  በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል በሚገኙ የኢትዮጲያ ጠቅላይ ግዛት ይባሉ የነበሩትን በርካታ ባህላዊ ታሪካዊና ሀይማኖታዊ ስፍራዎችን መጎብኘት የቻለው 17 ዓመቱ ገና 10 ክፍል ተማሪ ሳለ ነበር።

 

የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የመሪዎች ስብሰባ ኢትዮጵያ ውስጥ ሲካሄድ ታዬ ከጓደኞቹ ጋር በመሆን ኢትዮጵያን የሚያንፀባርቁ የተለያዩ ፅሁፎችን እና ፎቶግራፎችን በመሰብሰብ  በኤግዚቢሽን እንዲጎበኝ አድርጓል። ታዬ፣ 12 ክፍል እንደደረሰ ማትሪክ ለመፈተን በተዘጋጀበት ወቅት 1966 ማለት ነው አብዮቱ ፈነዳ። በዚህ ጊዜ የትምህርት ቤቱ ተማሪ ለሁለት ተከፈለ። ፈተናውን እንፈተን እና አንፈተን በሚል ውዝግብ ተፈጠረ። የተወሰኑት ተፈተኑ ሌሎች ደግሞ አለፋቸው ታዬም ካልተፈተኑት መካከል ነበር፡፡

 

     ከጃንሆይ መንግስት ለውጥ በኋላ

 

መንግስት ተቀየረ፡፡ የጃንሆይ መንግስት ወድቆ ግዜያዊ የደርግ አስተዳደር ተመሠረተ። በዚህ ወቅት ታዬ ኦጋዴን ስለኖረና ሶማሌኛ ቋንቋም ስለሚናገር በቀብሪዳሀር አውራጃሸኮችበምትባል የገጠር ከተማ በመንቀሳቀስ በእድገት በህብረት የእውቀትና የስራ ዘመቻ አባል ሆኖ ሳይማር ያስተማረውን ማህበረሰብ ማስተማር ጀመረ።ይህ ወቅት ደግሞ ሶማሊያ ኦጋዴንን ለመውረር እየተንቀሳቀሰች ያለችበትና አካባቢው በረሀብ ቸነፈር የተገረፈበት መጥፎ አጋጣሚ ነበር። አሁን ታዬና ጓደኞቹ ፊደል ማስቆጠሩን ትተው ስለጤና እና ስለ እርሻ ትምህርት መስጠት ጀመሩ። ከፍተኛ ለውጥ የታየበት ወቅትም ሆነ።

 

1967 እንዲህ አልፎ 1968 . ገባ። ይህ ወቅት ደግሞ የሀገራችን ፖለቲካ እጅግ የጦዘበት የኢህአፓና ሜኤሶን እንቅስቃሴም የተፋፋመበት በመሆኑ በነበረው ስሜት ስራን መስራት ያልቻለው ታዬ በላቸው ካምፑን ለቆ ወደ ቤተሰቦቹ ተመለሠ።  ወደ ቤተሰቦቹ ሲመለስ ግን ሁሉም ነገር ተለዋውጦ ጠበቀው። ሶማሊያ ያደገበትን አካባቢ ወራ ብዙ የእድገት በህብረት አባላት ተሰውተውና በጎርፍ ተወስደዉ ጠበቁት፡፡

 

1969 . ግን በህይወቱ ብርሀን የፈነጠቀበት ዘመን ሆነ። በተለይ 1996 በለውጡ ምክንያት ከትምህርታቸው የተሰናከሉ ተማሪዎች ተፈቅዶላቸው ማትሪክ እንዲፈተኑ ሆነ፡፡ ታዬም፣ የዚህ እድል ተጠቃሚ ነበርና ውጤት መጥቶለት አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ገባ። ባዮሎጂን ሜጀር ኬሚስትሪን ማይነር አድርጎ መማር ጀመረ። በዚህ ወቅት ግን ፖለቲካው የተጧጧፈበት ዘመን በመሆኑ ማን እንደሚገድል እንኳ ሳይታወቅ በየመንገዱ ወጣቱ ወድቆ የሚገኝበት ጊዜ ነበረ። ታዬ፣ በስጋት እስከ ጥር ከተማረ በኋላ የመማሩ ዋስትና አደጋ ላይ በመውደቁ ትምህርቱን አቋርጦ እህቱ ጋር ወደ ሀረር ተመለሰ።

 

በወቅቱ፣ በሀረርጌ ጠቅላይ ግዛት ስር የነበሩ በርካታ መምህራን በነበረው ጦርነት ምክንያት ለቅቀው ስለነበር 1 ደረጃ መምህራንን መቅጠር እንደሚፈልግ የሚገልፅ ማስታወቂያ ወጣና ተፈትኖ አልፎ በምዕራብ ሀረርጌ "መጣቀሻ" በምትባል ትንሽ ከተማ ማስተማር ጀመረ። በወቅቱ የየሀባ እንቅስቃሴ በአካባቢው ነግሶ ስለነበረ መሳሪያዎች ይዘረፋሉ፡፡ በዚህ ጊዜ በአካባቢው የሚገኙ መምህራን ሳይቀሩ ተለቅመው እንዲታሰሩ ተደረገ፡፡ ታዬምኢህአፓና ቅጥር ነብሰ ገዳይ ነህበሚል ምክንያት ያለምንም ጥያቄና ምስክር አሰበ ተፈሪ ጭሮ ማረሚያ ቤት ለአንድ ዓመት ያህል ታሰረ። እስር ቤት እያለም አብዮቱን በድላችኋል እና መካስ ስላለባችሁ ለእናት ሀገር ጥሪ ድራማ ስሩ ተብሎ ታዞም ድራማን ሰርቷል።

 

በመጨረሻም በነፃ ተለቅቆ፣ 1970 . ወደ ትምህርቱ ተመለሰና ኮተቤ መምህራን ትምህርት ኮሌጅ በእንግሊዘኛ ቋንቋ ተመርቆ `ደበሶበምትባል ትንሽ ከተማ 7 እና 8 ክፍል የእንግሊዘኛ ቋንቋ መምህር በመሆን መስራት ጀመረ። እያስተማረ እያለ ቀድሞ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ይማሩ የነበሩና ያቋረጡ ተማሪዎች መልሰው ትምህርታቸውን እንዲቀጥሉ ትዕዛዝ ተሰጠ። ታዬም የዚህ እድል ተጠቃሚ ሆኖ 1972 ዓም ተመልሶ ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ገብቶ ትምህርቱን ቀጠለ። በዩኒቨርሲቲ ቆይታው የነበረውን የስነፅሁፍ እውቀት ተጠቅሞ ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እና ለኢትዮጵያ ቴሌቪዥን አርቲክሎችን ይፅፍ ነበር።

 

       በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የጋዜጠኝነት ቆይታ

 

1974 . ታዬ የመጨረሻ ዓመት የዩኒቨርሲቲ ተማሪ ሳለ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የፕሮግራም አስፈፃሚነት የቅጥር ማስታወቂያ አወጣ። በወቅቱም ወደ 500  ሰዎች ተወዳድረው ታዬን ጨምሮ 5 ሰዎች አለፉ፡፡ በወር 285(በሁለት መቶ ሰማንያ አምስት ብር) እየተከፈለው በኮንትራት ሰራተኝነት በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ተቀጠረ። ታዬ "ከየ አቅጣጫው" የተሰኘ ፕሮግራምን ጨምሮ የተለያዩ ዜናዎችን ሰርቷል። ሳምንታዊ ፕሮግራምም ነበረው፡፡ አንድ ወቅት ከየአቅጣጫው በተሰኘ ፕሮግራሙ ላይ "በውሀ መሀል ተከባ ውሀ የተጠማች ሀገር" በማለት በወቅቱ በቢሾፍቱ አካባቢ የነበረውን የውሀ ችግር እስፍራው ድረስ በመሄድ በተንቀሳቃሽ ምስል አስደግፎ ያቀረበው ፕሮግራም እጅግ አነጋጋሪ ከመሆኑም በላይ አብዮቱን የሚቀለብስ አስተሳሰብ ያለው ጋዜጠኛ ነው ይሰቀላል ይገደላል ተባለ፡፡ አቶ ሀይለማርያም ጎሹ በሚባሉ በወቅቱ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ሀላፊ በነበሩ ጠንካራ ሰው አማካይነት ነገሮች ተፈትተው የታሰበለት ሳይሆን ጠንካራና ላመነበት ሟች መሆኑን ያስመሰከረበት አጋጣሚ ሆኖ አልፏል።

 

ታዬዓለም እንዴት ሰነበተች?” የሚል ፕሮግራም አስተባባሪ ሆኖም ሰርቷል።ቲቪ መስተዋትየሚባል ፕሮግራምም እንዲሁ ያዘጋጅ ነበር፡፡ በኋላም እያደገ መጥቶ የዜና ዋና አዘጋጅ መሆን ቻለ። በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን 6 ዓመታት  ድረስ በኮንትራት ከሰራ በኋላ 1979 . ቋሚ መሆንም ችሎ ነበር። ቋሚ ሲሆን ይከፈለው የነበረ ደመወዝም አድጎ 347 ብር ደርሶ ነበር። ይህ ክፍያ ደግሞ በዘመኑ የጋዜጠኝነት ታሪክ ትልቅ የሚባለው ነበር።

 

ታዬ፣ በዘመኑ አመራሮች ዘንድ በነበረው ተቀባይነት ከፍ እያለ በመምጣቱና ለስራ ባለው ተነሳሽነትና ፍጥነትም ስለሚደመሙ ኢሰፓኮ ሲመሠረት ሙሉ ዝግጅቱን በቤተ- መንግስት ተገኝቶ የሠራውም እርሱ ነበር። በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የማዘጋጃ ቤት ቆይታው ከነ ሀብታሙ በቀለ፣ ከነ የሺጥላ እና አሰፋ በቀለ ጋር የጠበቀ ጓደኝነት ነበረው። እንደ ተወርዋሪ ኮከብ እያበራ ለኢትዮጵያ ቴሌቪዥን አገልግሏል። ኡጋዴን አካባቢ በነበረው ጦርነት እና 1977 በነበረው ድርቅ የተጎዱ ወገኖቹን ለማቋቋም በነበረው ሂደት ታዬ በሙያው ትልቅ ተሳትፎን አድርጓል።

 

በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በነበረው (ዘጠኝ) ዓመት ጉዞ ወደ ሀሰብ፣ ወደ ትግራይና ወደ ኤርትራ እንዲሁም በደቡቡ የሀገራችን ክፍል በድርቅ በተጎዱ አካባቢዎች በመዘዋወር የተለያዩ መድረኮችን ያዘጋጅ ነበር። በውጭ ሀገር ሳይቀር እየተንቀሳቀሰ የሚሰራ ጋዜጠኛ ነው። ኢህአዴግ እስኪገባ ድረስ በነበረው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ቆይታው ከሺህ በላይ የሚሆኑ ዜናና ፕሮግራሞችን በአድማጭ ተመልካቹ  ልብ ውስጥ እና የቴሌቪዥን አርካይቭ ላይ ማስቀመጥ የቻለ ሰው ነው። የቤተመንግስት ሪፖርተርም በመሆን በፓርላማ የሚካሄዱ ሁነቶችን ወደ ህዝቡ የሚያደርስ ነበር። የቤተመንግስት ጉዳዮች ዘጋቢነት የስራ ግዜው አልጋ በአልጋ አልነበረም፡፡ ስፍራው ከፍተኛ ጥንቃቄን የሚፈልግ በመሆኑ ታዬም በአንድ ወቅት ካሜራ ማኑ የፈጠረውን የምስል መበላሸት ቆርጦ ለማውጣት ሲል የጓድ መንግስቱ ሀይለማርያምን ንግግር ቆርጦ በመግጠሙ እርሱ (50)ሀምሳ ብር የቅርብ አለቃው የነበረው አስቻለው ደምሴ ደግም (100)መቶ ብር እንዲቀጡ ተደርገዋል።

 

1957 . የተቋቋመው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የተመሠረተበትን 25ኛውን የብር ኢዩቤልዩ በዓል ሲከበር ሲጀመር ጀምሮ የነበሩትን ትላልቅ ሰራተኞች አግኝቶ በማነጋገር ጣቢያው ሲጀመር ምን ይመስል እንደነበርና 25 ዓመታት ውስጥ ያሳየውን ለውጥ ፍንትው አድርጎ የሚያሳይ ትልቅ መፅሄት አዘጋጅቶም ነበር።  በዘመኑ ተከስቶ በነበረው ድርቅ ከተለያየ የሀገራችን ክፍሎች ተፈናቅለው የነበሩ ዜጎችን ከእርዳታ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ጋር በመሆን የማስፈርና የማቋቋም ስራዎችን የሠራበትን አጋጣሚ ታዬ በላቸው አለቃ በነበረበት ወቅት በስሩ የሚገኙ ጋዜጠኞችን የሚያግዝ አዳዲስ ጋዜጠኞች ሲቀጠሩ ሙያዊ ድጋፎችን ይሰጥ የነበረ እና ጎበዝ ጋዜጠኞችን አፍርቻለሁ ይህንንም ዛሬ ላይ ስመለከት እኮራበታለሁ ይላል።

 

የጋምቤላ ባሮ ድልድይ ሲመረቅ፤ የአሰብ መንገድ ለአገልግሎት ክፍት ሲሆን፤ የአሰብ ኤርፖርት ሲመረቅ፤ አየር ሀይል እና ባህር ሀይል ሲመረቅ ሁሉ በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች እየተንቀሳቀሰ ዘግቧል። ታዬ በላቸው፣ በዚያን ዘመን live/ ቀጥታ ስርጭት/ የሚያቀርብ ደፋር ጋዜጠኛም ነበር። በውጥረት ውስጥ ስራዎችን በፍጥነት በመስራት የሚታወቅ በመሆኑ በጣቢያው የሚሰጠው የስራ አፈፃፀም ውጤት ጥሩ ነበር። በዚህም የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ከጀርመን ሀገር ጋር በነበረው መልካም ግንኙነት ስኮላር ሺፕ ይሰጥ ነበርና ታዬም በበርሊን ተገኝቶ የጋዜጠኝነት ሙያ ስልጠናን ማግኘት ችሏል። በራሺያ በእንግሊዝና በጀርመን ወታደሮች ይጠበቅ የነበረው የበርሊን ግምብ ሲፈርስ እና ሁለቱ የጀርመን ሀገሮች ተዋህደዉ ጀርመን አንድ ስትሆን የተመለከተ በስፍራው ስለነበረ  ለዘመናት ተራርቀው የነበሩ ቤተሰቦች ሲገናኙ የነበረውን ስሜት የተጋራ የአይን እማኝም ነበር

 

        ከደርግ መንግስት መውደቅ በኋላ

 

ኢህአዴግ እንደገባ ግንቦት 19 ቀን1983 ማለት ነዉ የምሽቱ የጣቢያው አስፈፃሚ ከነበሩት አንዱ ታዬ በላቸው ነበር። ሀገር ቀልጧል በየቦታው የሚሰማው የጥይት ድምፅ ነው፡፡ ግንቦት 20 ቀን ኢህአዴግ ከተማዋን ሙሉ በሙሉ ሲቆጣጠር ታዬ 3ቀን ያህል ከቤተሰቦቹ ጋር ሳይገናኝ የቆየበት አጋጣሚ ነበር። ከሳምንት በኋላ ወደ ስራ ገበታቸው እንዲመለሱ ትዕዛዝ ተሰጣቸውና ተመለሱ። በወቅቱ የቡርቃ ዝምታ መፅሀፍ ደራሲ ተስፋዬ ገብረአብ ሀላፊ ሆኖ ነበር። ከአንድ ሳምንት ስራ በኋላ ከሰኔ 24 ሽግግር መንግስት በፊት መሆኑ ነውአማረ አረጋዊ፣ በረከት ስምኦንና ተስፋዬ ገብረአብየሚመሩት ትልቅ ስብሰባ ተካሂዶ ለደርግ መንግስት በጣም የሰሩ ጋዜጠኞች ከስራ ገበታቸው እንዲታገዱ ስማቸው ከተዘረዘሩት መካከል አንዱ ታዬ ነበር። ታዬና ወደ 14 የሚደርሱ ሰራተኞች ከስራ ገበታቸው ተባረሩ። ከፕሬስ እነሙሉጌታ ሉሌከራዲዮ እነሀይሉ ወልደፃዲቅንጨምሮ ወደ 64 የሚሆኑ ሰዎች በወቅቱ ከስራ ተባረዉ ነበርና ምን እናድርግ? በሚል መሰባሰብ እና መመካከር ጀመሩ። በኋላ አራት ኪሎ ባለውሲፒኤክስ አቀረቡ። ከብዙ ምልልስና ክርክር በኋላ ወደ ስራ ገበታቸው እንዲመለሱ ተወሰነላቸው። ነገር ግን አብሮ መሰራቱ የህይወት ማጣት ዋጋን ሊያስከፍል ስለሚችል የፖለቲካ ውሳኔ ተሰጥቷቸው ጡረታው የደረሰ ጡረታው እንዲከበርለት መስራት የሚችለው ደግሞ ከማስታወቂያ ሚኒስቴር ውጭ በየትኛውም ቦታ ገብተው መስራት ይችላሉ የሚል ደብዳቤ ተሰጣቸው። ከዚህ በኋላ ግን ታዬ በላቸው በኢትዮጸጵያ ቴሌቪዥን የነበረው ህይወት አከተመለት።

 

           በጦቢያ መጽሄት ከሪፖርተርነት እስከ ዋና አዘጋጅነት

 

ከኢትዮጲያ ቴሌቪዥን መባረር በኋላ፣ ታላላቅ የሚባሉ ባለሞያዎች ተሰባስበውጦቢያየምትባል  መፅሄትን ማዘጋጀት ጀመሩ። ጊዜውም 1984 ነበር፡፡ ጋሽ ሙሉጌታ ሉሌ የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ ሆኖ ታዬን ጨምሮ በርካታ ከስራ ተሰናባቾች የተካተቱባት በሳምንት 60 ሺህ እስከ 100 ሺህ ኮፒ የሚታተምላትጦቢያየምትባል ብዙ አንባቢያንን መያዝ የቻለች መፅሄት ማሳተም ቻሉ። ግና አልተኛ ባሉት ጠላቶቻቸው "ጦቢያ" የሚለው መጠሪያ "ጦሩ ቢዋጋ ያሸንፋል" የሚል ትርጓሜ የያዘ ነው የሚል ፕሮፓጋንዳ ተከፍቶባቸውም ነበር። ያም ሆኖ ታዬ በላቸው በጦቢያ መፅሄት ታሪክ ከሪፖርተርነት ጀምሮ እስከ ዋና አዘጋጅ በኋላም እስከ ቡድን መሪነት ለዘጠኝ አመታት ሰርቷል። በዚህ 9 ዓመት ቆይታውም ወደ አራት ያህል ጊዜ ታስሮ ተፈቷል። ታዬ በፊት መፅሄት የነበረችና በኋላም ጋዜጣ መሆን በቻለችው ጦቢያ ላይ የመፅሄቷ አዘጋጅ ሆኖም ታላላቅ የሚባሉ ሰዎች ጋር ቃለ ምልልስ በማድረግ ይፅፍ ነበር። ኤችአይቪ ኤድስ መከላከልን በተመለከተ ህይወት እንታደግ የሚል ፕሮጀክት ቀርፀው የዚህ አምድ አዘጋጅ በመሆንም ሰርቷል። የስፖርትና የህግ ነክ ፅሁፎች ከመውጣታቸው በፊት የማየቱን ስራም ይሰራ ነበር።

 

1987 . በሙባረክ ግድያ ዙሪያ በፃፈው ፅሁፍ ማእከላዊ ታስሯል። ሀሰተኛ ዜና ፅፈሀል በሚል ጥቅማቸው የተነካ ሰዎች በሙሽርነት ጊዜው ሳይቀር የጫጉላ ግዜውን ሀዋሳ በክስ ላይ እንዲያሳልፍ አድርገውታል።ኤርትራና ትግራይ ከኢትዮጵያ ቢገነጠሉ ካንሰር ናቸው አያስፈልጉምየሚል መንፈስ ያለው በፕሮፌሰር ይልማ የተፃፈን የእንግሊዝኛ ፅሁፍ ወደ አማርኛ ተርጉሞ በማቅረቡ ካንሰር ብሎ ተሳድቧል ተብሎ ትልቅ መነጋገሪያ ሆኖ ለሶስት ወራት ታስሮም 5000 ብር ዋስ የተፈታበት አጋጣሚ ነበር። ለመጨረሻ ግዜ 1990 . አካባቢ ኢሲኤ በምስራቅ ኢትዮጵያ አካባቢ ያለው የፀጥታ ሁኔታ አስጊ ስለሆነ ለሰራተኞቹ ከቤታችሁ እንዳትወጡ ነገሮች ከከፉ ወደመጣችሁበት እንመልሳችኋለን በማለት ከአዲስ አበባ ከተማ እንዳይወጡ የሚያሳስብ ማስጠንቀቂያ የሰጠበትን መግለጫ ወደ አማርኛ ተርጉሞ በማቅረቡ ህዝቡን አሸበረ ተብሎ ከከፍተኛ ድብደባና ስቃይ ጋር  ለሶስት ወር ማእላዊ ለአራት ወራት ደግሞ ማረሚያ ቤት ታስሯል።

 

ታዬ ጋዜጠኛ በመሆኑና እውነታውን በመፃፉ ብቻ በተለያዩ ግዜያት ከአስር ጊዜ በላይ ታስሯል። እስሩ ሲበዛበት ይበልጥ እንደ ብረት እያጠነከረው ይመጣል እንጂ በህይወቱ ተስፋ የቆረጠበት ግዜን አያስታውስም። በማያውቀውና እርሱን ተጠያቂ በማያደርገው ሁሉ ቡድኖች ተደራጅተው ሲያጠቁት እጅ ከመስጠት ይልቅ ያለ ጠበቃ የመመከት አቅሙን ለማጎልበት ህግን ተምሮ በዲግሪ ተመርቋል፡፡ በጀርመን ከተማረው ኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ በተጨማሪ በአዲስ አበባ ፕሪንቲንግ ሚዲያን ተምሮ ዲግሪውንም ይዟል።

 

1993 አካባቢ ትምህርቱን ከጨረሰ በኋላ ከጦቢያ ለቀቀና ከሌሎች  አምስት ጓደኞቹ ጋር በመሆን እያንዳንዳቸው አምስት ሺህ ብር በማዋጣት ልሳነ ህዝብ መፅሄትና ጋዜጣን ማሳተም ጀመሩ። መፅሄቷ እስከ 1997 ድረስ ከታተመች በኋላ 97 ምርጫ ሲደርስ እንዳይታተሙ ለብርሀንና ሰላም ከተፃፈባቸው  መፅሄቶች አንዷ በመሆኗ እንዲቆም ተደረገ።

 

ከዚህ በኋላ ግን ታታሪውና ለሞያው ብዙ ዋጋን የከፈለው ጋዜጠኛ ታዬ በላቸው የጋዜጠኝነት ስራ በቃኝ ብሎ በዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ ስኮላር ሺፕ አግኝቶ መማር ጀመረ።  ግና ጋዜጠኝነት ከህይወቱ ጋር የተጋመደው ታዬ በመማር ላይ ሳለሪሊያንስ አፍሪካየሚባል ፕሮጀክት መጥቶ ፕሮጀክቱ በሚያሳትመው ጋዜጣ ላይፍሊራንሰርሆኖ መስራት ጀመረ። እየሰራ የተማረውን ትምህርቱን ሲጨርስ ጎበዝ ተማሪም ስለነበር በከፍተኛ ማእረግ ተመርቆ ዋንጫና የወርቅ ሜዳሊያን ያጠለቀ ጀግና ነበር። ዩኒቨርሲቲው ወደ ሼር ካምፖኒ ሲቀየር በተማሪዎች ተወክሎ የቦርድ ፀሀፊም ሆኖ አገልግሏል።

 

የአዲስ አበባ ንግድ ዘርፍ ማህበራት /ቤት በወር የሚታተም ጋዜጣ ላይ የታክስ ነክ ጉዳዮች ላይ አርቲክሎችን በመፃፍ ለአምስት ዓመት ያህል ሰርቷል። የግል ኢንዱስትሪዎች ማህበር ደግሞ በየ ሁለት ወር የሚታተም አምራች ኢንዱስትሪው የሚል መፅሄትና ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ሆኖም ሰርቷል።

 

በኢትዮጵያ የሚዲያ ታሪክ ውስጥ በህትመቱም ሆነ በኤሌክትሮኒክሱ ዘርፍ በርካታ ስራዎችን የሠራና ዛሬም በመስራት ላይ የሚገኘው ታዬ በነፃው ፕሬስ 30 ዓመት ታሪክ ጉዞው ውስጥየሰላም ጋዜጠኝነትየሚባል ተልእኮ ከተሰጣቸው አንዱ ሆኖ በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል ያለው ጦርነት እንዲቆም ትልቅ ጥረት ቢያደርጉም ጥረታቸው ሳይሳካ በመቅረቱ ግን ለዘመናት ሲቆጭ እንደነበረ ይናገራል።ዛሬ ለውጡ ይዞት ከመጣው አንዱ የኤርትራና የኢትዮጵያ እርቅ መሆኑ ደግሞ ያስደስተዋል።

 

         ከኢህአዴግ መንግስት መዉደቅ በኋላ

 

ታዬ በላቸዉ ከለውጡ በኋላም በሞያዉ የተለያዩ የኮሚቴ እና የግል ስራዎችን በመስራት  ሀገሩ በፈለገችበት ሁሉ በመሰማራት ላይ ይገኛል፡፡ 2010 ለውጥ በኋላ የሚዲያ አሳሪ ህጉ እንዲሻሻል በፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ በኮሚቴነት ከተዋቀሩት አንዱ ሆኖ በህግም በጋዜጠኝነትም ሞያህ ሀገርህ ትፈልግሀለች ተብሎ ስለታመነበት ያለምንም ክፍያ 11 ወር ከግብረ ሀይሉ ጋር በመሆን በተለይ የመገናኛ ብዙሀን አዋጅን አራት ቦታ ከፋፍሎ የማስቀመጥ ስራዎችን ሰርቷል።

 

ታዬ በሲዳማ ሪፈረንደም ወቅት ታዛቢ በመሆንና በስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ እና ድህረ ምርጫ ተንቀሳቃሽና ተቀማጭ ታዛቢ በመሆን በአማራ ክልልና በአዲስ አበባ ዙሪያ ወደ 2.7 ሚሊዮን ለሚሆኑ ሰዎች የምርጫ ስነምግባር ስልጠናን ሰጥቷል።

 

አሁን ላይ የተለያዩ የህግ ጉዳዮችን በማማከርና በጋዜጠኝነት ሞያ ላይም የተለያዩ አጫጭር ስልጠናዎችን  በመስጠት እና በማስተማር ስራ ላይ ይገኛል። ወደ NGO ገብቶ “vision Ethiopian Congress  Democratic Party” በሚባል የሲቪክ ድርጅት ውስጥ የተመራቂ ተማሪዎች መፅሄትን በማዘጋጀት፤ ህግ ነክ የሆኑ አጫጭር ኮርሶችን በመስጠትና የፀረሙስናና የስነምግባር መኮንንም ሆኖ በመስራት ላይ ይገኛል ታዬ ህግና ጋዜጠኝነትን እያጣጣመ አሁን በስራ ላይ አርባ ዓመታት ሞላው፡፡

 

          የትዳር ህይወት

 

ታዬ ትዳር የመሠረተው 1987 . ሲሆን ከዛሬዋ የትዳር አጋሩ / አበራሽ ጋር የተዋወቁት 1981 ነበር። በወላጅ እናቱ ከፍተኛ ግፊት እርሱ ሳያውቅ ሙሉ የጥሎሽ ወጪውን ሸፍነውና ጓደኞቹ እነ ሙሉጌታ ሉሌ እቁብ ሰብስበው የቤት እቃ አሟልተው ሞቅ ባለ ሰርግ ነበር ትዳር እንዲመሰርት ያደረጉት።

 

በትዳር በቆየባቸዉ 27 ዓመታት እድሜ አንድ ወንድና አንድ ሴት ልጆችን ማፍራት ችለዋል፡፡ ሴት ልጁ ምልክት ታዬ ማስተርሷን እየተማረች ሲሆን በአንድ ትምህርት ቤት ውስጥ የኮምፒውተር አሲስታንት መምህር ነች።

 

መዝጊያ ይህ መዝጊያ የተወዳጅ ሚድያ እና ኮሚኒኬሽንን አቋም የሚንጸባረቅበት ነው፡፡

 

ታዬ በላቸው መልካ በሳል ጋዜጠኛ ነው፡፡ በሳል ብቻ ሳይሆን ለሙያው የተለየ ክብር አለው፡፡ ታሪኩን ስናነብ የምንረዳው ይህንን ነው፡፡ ታዬ በቲቪ እና በህትመት ሚድያ ላይ ሙሉ አቅሙን በማሳየት ችሎታው እምን ድረስ እንደሆነ አሳይቷል፡፡ ፈታኝ በሆነው የጋዜጠኝነት ህይወት ውስጥ ሲያልፍ አንድም ቅር የሚለው ነገር የለም፡፡ ሙያውን ከልቡ የሚወድ ሰው ለሙያ የሚከፈል ዋጋ እምን ድረስ እንደሆነ ያውቃል፡፡ ታዬም ከእነዚህ ተርታ ይመደባል፡፡ ከልጅነቱ ጀምሮ መሆን የሚፈልገውን ማሳካት ችሏል፡፡ እርሱ ህልሙን ሲያሳካ በኢትዮጵያ የጋዜጠኝነት ታሪክ ውስጥ ደግሞ አንድ ትልቅ ክፍተት እና ግዙፍ አሻራ ለማኖር ችሏል፡፡ 1970ዎቹ አጋማሽና 1980 ዎቹ መጀመሪያ ላይ ቲቪ የከፈተ የታዬን በሳል መርማሪ ዜናዎች መመልከት ይችላል፡፡ ታዬን በጦቢያ መጽሄት አዘጋጅነቱ የሚያውቁት ኢቲቪ መስራቱን ላይሰሙ ወይም ላያነቡ ይችላሉ፡፡ ታዬ ግን በቃኝ ሰለቸኝ ሳይል 1000 በላይ ዜና እና ፕሮግራሞችን 9 አመታት ኢቲቪ አየር ላይ ማዋል የቻለ ነው፡፡ ስለ ሀገራችን የጋዜጠኝነት ታሪክ ስናነሳ እንደ ታዬ በላቸው አይነት አርቆ ተመልካች የሚድያ ሰዎች ብዙ አይነሱም፤፡ በጋዜጣ በቲቪ በሬድዮ ታሪካቸው በደማቅ ብእር ሲጻፍ አናይም፡፡ ታዬ ግን ባሳለፋቸው 40 የጋዜጠኝነት ልምዱ ብዙ እውቀት ያካበተ ብዙ ሊያሰለጥን የሚችል ጠንካራ ሰው ነው፡፡ 30 አመት ስለሞላው የሀገራችን የነጻ ፕሬስ ታሪክ ስናነሳ  ታዬ በቀዳሚነት ስማቸው ከሚነሳ አንዱ ነው፡፡ ጉምቱ የሚድያ ሰዎች ከሚባሉት ከእነ ሙሉጌታ ሉሌ ጎሹ ሞገስ እንዲሁም አጥፍሰገድ ይልማ ጋር የመስራት እድል የነበረው ታዬ ከእነርሱም በርካታ እውቀቶችን በመቅሰም ለሌሎች ለማካፈል የቻለ ሰው ነው፡፡ የዚህ  ዊኪፒዲያ መስራች፣ ታዬ በላቸውን ሲያውቀው 27 አመት አስቆጥሯል፡፡  ታዬን 27 አመት እንደማወቁ መጠን ሲገልጸው ታናናሾችን ለማበረታታት እና መጪ ጊዜያቸውን ብሩህ በማድረግ የተካነ ነው ይለዋል፡፡ በዚህ ዊኪፒዲያ አዘጋጆች እምነት ታዬ በላቸው በኢትዮጵያ የጋዜጠኝነት ታሪክ ውስጥ የራሱን ትልቅ አሻራ ያኖረ ለስራ የተፈጠረ ህልሙን የኖረ አሁንም በትጋት የሚታወቅ ተወዳጅ እና ታታሪ ሰው ነው፡፡ ታሪኩ በዚህ መልክ ቀርቦ ለመጪው ትውልድ እንዲሰነድ ሀሳብ ስናደርግም  ዋናው ግባችን ደክመው ያልታወቁ ሰዎች እንዲታወቁ ለማድረግ ነው፡፡ ይህን በማድረጋችን ትልቅ ሃላፊነት እንደተወጣን እንቆጥረዋለን፡፡ ደግሞም ታዬ የሚገባው ስለሆነ በዚህ ጥንካሬው እንዲቀጥል እንመኛለን፡፡ / ይህ ጽሁፍ በጋዜጠኛ ዘቢባ ሁሴን እና በጋዜጠኛ እዝራ እጅጉ የተሰናዳ ሲሆን በተወዳጅ ሚድያ የፌስ ቡክ ገጽና በዚህ ዊኪፒዲያ ላይ ዛሬ እሁድ ህዳር 26 2014 ሊወጣ ቻለ፡፡ አስፈላጊው ማሻሻያ እየተደረገበትም በየጊዜው ሀሳቦች እየታከሉበት እንዲወጣ ይደረጋል

አስተያየቶች

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች