ተወዳጅ ሚድያ እና ኮሚኒኬሽን የቴአትርና የስነ-ጽሁፍ ሰዎችን ታሪክ ከአንጋፋ እስከ ወጣት በሚል ሀሳብ የብዙዎችን ታሪክ እያሰባሰበ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ወደፊትም የቴአትር እና የስነ-ጽሁፍ ባለሙያዎችን ታሪክ ራሱን ችሎ ደረጃውን በጠበቀና ጠንካራ በሆነ ሽፋን/hard
cover/ ኢንሳይክሎፒዲያ
ሊታተም
እንደሆነ
ይታወቃል፡፡
እስከዚያ
ድረስ
ታሪካቸው
በዚህ
ዊኪፒዲያ
እና በተወዳጅ ሚድያ የፌስ ቡክ ገጽ ላይ ከሚነገርላቸው መካከል ጸሀፌ-ተውኔት አያልነህ ሙላቱ አንዱ ነው፡፡ ግለ-ታሪኩን ዘቢባ ሁሴን እንደሚከተለው አጠናክራዋለች፡፡
በሃገራችን የትያትር ታሪክ ውስጥ ስማቸውን በደማቅ ከፃፉት ከያንያን መካከል ስሙ ይጠራል፡፡ ከዩኒቨርሲቲ መምህርነት እስከ ባህል ማዕከል ዳይሬክተርነት ሀገሩን አገልግሏል፡፡ በተለያዩ የትርጉምና አዳዲስ ወጥ የፈጠራ የስነ -ፅሁፍ ትሩፋቶችን አበርክቷል፡፡ በህዝብ ለህዝብ የባህል ኪነ-ጥበብ ዝግጅት ወቅት የአንበሳውን ድርሻ ከተወጡት መካከል አንዱ ነበር፡፡ ፀሃፌ ተውኔት፣ ገጣሚ ፣ባለቅኔም ነው፡፡ ብዙ ወዳጆቹ፣ አድናቂዎቹና ከእርሱ የተማሩቱ ሁሉ ዛሬም ድረስ ጋሼ እያሉ ይጠሩታል፡፡ ብዕረኛው አያልነህ ሙላቱ አበጄ፡፡
ውልደትና እድገት
የተወለደው ህዳር 12 ቀን 1941 ዓ.ም ጓጃም ውስጥ በምትገኝ አንዲት የገጠር መንደር ነው። እርሱ ሲወለድ ወላጅ አባቱ የምስለኔነት ሹመት ላይ ስለነበሩ ያደገው የሹም ልጅ እየተባለ ነበር። እድሜው ለትምህርት ሲደርስ እዚያው በተወለደበት መንደር አብነት ትምህርት ቤት ገብቶም ነበር። በእርግጥ እንደዘመኑ ልጆች ውዳሴ ማርያምን በዜማ ጮኋል። ዳዊትንም ደግሟል። ግን አልዘለቀበትም። ወላጆቹ ዘመናዊ ትምህርት እንዲቀስም ስለፈለጉ ዳንግላ ከተማ "መንገሻ ጀምበሬ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት" አስገቡት። ይሁንና ይህ ትምህርት ቤት ከመኖሪያ ቤቱ 17 ኪ.ሜ ገደማ ርቀት ላይ በመሆኑና በዘመኑ እንደዛሬው ምግብ መቋጠርና መጫሚያ ማድረግ ስላልነበረ በለጋ እድሜው ረሀቡንና የሚወጋውን እሾህ ሊቋቋመው አልቻለም። ወይ እንደሌሎቹ አኮፋዳን አንግቦ የሚያጓርሰው አይፈልግ አንድም የሹም ልጅ በሌላም በኩል የዘመናዊ ትምህርት ተማሪ። በዚህም የተነሳ በትምህርቱም ሰነፍ ከሚባሉት እንደሚመደብና እንደርሱ ትምህርትን የሚጠላ ያለ እንደማይመስለው ዛሬ ላይ ባገኘው አጋጣሚ ሁሉ ይናገራል።
ታዲያ የትምህርት ጣዕሙና ጥቅሙ አልገባው ያለው ይህ ብላቴና አልማርም እምቢኝ አሻፈረን ብሎ አመፀ፡፡ ልጃቸው ማለፊያ ፀሀፊ ሆኖ ማየትን ያልሙ የነበሩና ፊደል ያልቆጠሩ አባቱ ግን እዚያው ትምህርት ቤት ውስጥ የሚበላው እየቀረበለት በእግር ብረት ታስሮ እንዲማር ፈረዱበት። በአባቱ ያላሰለሰ ጥረት ዕድሜውም ከፍ እያለ ሲመጣ ትምህርት የመቀበል ፍላጎቱም በመጠኑ እየተሻሻለ ሄደ። አሳምሮ ማንበብና መፃፍንም ቻለ። ከአባቱም አልፎ ለአካባቢው ገበሬዎች የአቤቱታ ማመልከቻዎችን ይፅፍ ጀመረ።
አያልነህና የሥነ-ፅሁፋ ጅማሮ
ለአያልነህ የስነፅሁፍ ፍቅር ማደርና ወደሱም የመሳብ ፍላጎት እንዲኖረው በእግር ብረት አስረው እንዲማር ያደረጉት አባቱ ናቸው። ማንበብም ሆነ መፃፍ የማይችሉት እኚህ አባቱ መፅሀፍ ሲነበብ መስማት በእጅጉን ይወዱ ነበርና ከጣሊያን ወረራ ጀምረው በርካታ መፅሀፍትን ሰብስበዋል። አያልነህም ባለችው የእረፍት ሰዓት ሁሉ ቤታቸው ውስጥ ተሰብስበው ቡና ለሚጠጡ ሰዎች በቀን 3 ግዜ ድምፁን ከፍ አድርጓ እንዲያነብ ይገደድ ነበር። በተለይ መፅሀፍ ቅዱስን ለ3 ያህል ጊዜ መላልሶ አንብቦታል። አርዓያን፣እንቅልፍ
ለምኔን፣እንደወጣች
ቀረችን፣አግአዚንና
ጦቢያን
ጨምሮ
ሌሎች
ዘመኑን
ተንተርሰው
የተፃፉ
የታሪክ
መፅሀፍትና
ተረቶችን
አንብቦ
የጨረሰው
ይጠቅመኛል
ብሎ ሳይሆን የአባቱን አለንጋ ፈርቶ ነበር። በኋላ ግን የእውነትም በስነ ፅሁፍ ፍቅር እየተለከፈ መጣ። የ3ኛ ክፍል ተማሪ ሆኖ የራሱን ግጥሞች መፃፍና ማንበብን ጀመረ። የወንድ ጓደኞቹም ለሚያፈቅሯት ሴት የፍቅር ደብዳቤ እየለመኑ ያፅፉትም ጀመር፡፡
በዳንግላ የመጀመሪያ ትምህርቱን አጠናቆ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ለመማር ወደ ደብረ ማርቆስ አመራ። በደብረ ማርቆስም “ንጉስ ተክለ ሃይማኖት ትምህርት ቤት” ገባ። እዚህ ለኪነጥበብ ይበልጥ ትኩረት የሰጠበትም ጊዜ ሆነ። ሰባቱን የጎጃም አውራጃዎች ያሳተፈ አንድ ፌስቲቫል ሲዘጋጅ አያልነህ ለዘፈን መግቢያ የሚሆን አንድ አጭር ጭውውትን ፃፈ። በዚህም ለመጀመሪያ ግዜ አይቶት የማያውቀውን ገንዘብ (70 ብር) ተሸለመ። ከዚህ በኋላማ ማን ይቻለው; የትምህርት ቤቱን የቴአትር ክበብ አቋቋመ። ተውኔት ፅፎ ለእይታ አቅርቦም ባገኘው ገቢ የእግር ኳስ ቡድን አቋቁሞ ኳስና ማልያ ገዝቶ አስረክቧል።
ጋሽ አያልነህና የዩኒቨርሲቲ ቆይታው
አያልነህ ሙላት በ1958 ዓ.ም የያኔው ቀዳማዊ ሀይለ ስላሴ ዩኒቨርሲቲ የዛሬው አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ማለት ነው በዕደ ማርያም ትምህርት ቤት ገባ። ይሄኔ ጓበዝ ተማሪ ብቻ ሳይሆን የተዋጣለት የሥነ-ፅሁፍ ሰው ለመሆን ቻለ። በተለይ "ኢትዮጵያዊው ሼክስፔር ማን ነው;" በሚል ርዕስ በዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች መካከል የግጥም ውድድር ተካሂዶ 1ኛ ሲወጣ የተሸለመው ዋንጫ ትልቅ ብርታት ሆኖት ነበር።
የ1ኛ ዓመት ተማሪ እያለ "ቶርች" የተባለች የትምህርት ክፍሉ ተማሪዎች ጋዜጣ ዝግጅት የቦርድ ኣባል የመሆን እድልንም አግኝቶ ነበር። 2ኛ አመት እንደደረሰ በዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች የተቃውሞ ሰልፍ ላይ ተሳታፊ በመሆኑ በአድማ በታኞች ተደብድቦ ለሁለት ወራት ያህል በፖሊስ ሆስፒታል ቆይታ አደረገ። ከዚህ በኋላ ግን ወደ ዩኒቨርሲቲ መመለስ አልፈለገም፡፡ በኮተቤ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የ10ኛና የ11ኛ ክፍል የአማርኛ ቋንቋ አስተማሪ ሆኖ ተቀጠረ።
በኮተቤ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የነበረው ቆይታ
በዚህ ጊዜ ነበር ከታላቁ ደራሲ ከአቶ መንግስቱ ለማና ከተከበሩ ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ ጋር በቅርብ ለመተዋወቅ የቻለው። አጋጣሚውም እንዲህ ነበር፡፡ የኮተቤ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ወደ መምህራን ማሠልጠኛነት ሲቀየር በተዘጋጀው ሥነ ሥርዓት ላይ "የቱ ነው ተማሪ" በሚል ርዕስ ሙዚቃዊ ትርኢት አዘጋጅቶ በዚህ ፕሮግራም ላይ ንጉሰ ነገስቱ ከመላ ካቢኒያቸው ጋር ተገኝተውም ነበር፡፡ በዚህ ቀን አቶ መንግስቱ ለማ ይህን በሳል ስራ ተመልክተው እንደልጃቸው አቅርበው በሳል የሥነፅሁፍ ዕውቀታቸውን ከአባቱ ቀጥለው መሠረቱን ያጠነከሩለት፡፡
እውቅናና
ዝናን
ያቀዳጀውን
የቴአትር
ጥበብ
መሥመሩን
ያገኘው
እና አንተ ገጣሚ አይደለህም ግጥሞችህ ውስጥ ገፀ ባህርያት ሲንቀሳቀሱ ይታዩኛልና አንተ መሆን ምትችለው ፀሀፌ ተውኔት ነው በማለት መክሊቱን እንዲያውቅ ያደረጉትም እኚሁ ታላቅ የስነ ፅሁፍ ሊቅ እንደነበሩ ይናገራል።
አቅሙን በደንብ የተረዱት አቶ መንግስቱ የያኔው የድርሰት ማህበር ዋና ፀሀፊ ነበሩና በማህበሩ አማካይነት ነፃ የትምህርት ዕድል አግኝተውለት ወደ ሶቭየት ህብረት(ወደ ዛሬዋ ሩሲያ) ሄዶ በዓለም ታዋቂ በሆነው በሞስኮ የመንግስት ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነት ትምህርቱን መከታተል ችሏል፡፡
ጉዞ ወደ ሶቭየት ህብረት (የዛሬዋ ሩሲያ)
ሞስኮ ለአያልነህ ወድዷት የሚኖርባት ከተማ ነበረች፡፡ ከፑሽኪን ቅድመ አያት ሀገር ከኢትዮጲያ በመምጣቱም ክብር ነበረው፡፡ ወጣቱ ገጣሚ የሚል ስምም ተከትሎት ነበር። በሞስኮ ሬዲዮ ጣቢያ የአማርኛው ክፍለ- ጊዜ በሳምንት ሁለት ቀን "የገጣሚው ደብተር" የተባለ ዝግጅትን ለ6 ዓመታት ይመራም ነበር። ጎን ለጎንም በትምህርቱ ጠንክሮ ነበርና በጥሩ ውጤት አጠናቆ በ1967 ዓ.ም ሁለተኛ ዲግሪውን ተቀበለ። ሶስተኛ ዲግሪውን ሊቀበል ጥቂት ጊዜ ሲቀረው ግን በዘመነ ደርግ የባህል ሚኒስተር ቋሚ ተጠሪ የነበሩት ሎሬት ፀጋዬ ገብረመድህን በአደረጉለት ጥሪ መሰረት ድግሪውንም፤ በሞስኮ ያፈራውን ትዳርም ሆነ የሬዲዮ ዝግጅቱን፤ በፕሮግረስ ማተሚያ ቤት በቋሚ ተቀጣሪነት ይሰራው የነበረውን የትርጉም ሥራ እርግፍ አድርጓ በመተው ሀገሬን ብሎ ተመለሰ።
አገር በለጠብኝ
“ማን እንደ ሃገር” እንዲሉ ማቄን ጨርቄን ሳይል ወደ ሃገሩ የተመለሰው አያልነህ በሎሬት ፀጋዬ ገብረመድህን ጥያቄ በባህል ሚኒስቴር ውስጥ ሥራ ጀመረ። የቴአትር ጥበባት ድርጅት የተሰኘ አዲስ መምሪያ መዋቅር አዘጋጅቶ ካፀደቀ በኋላ የመምሪያው ተጠሪ ሆኖ ተመደበ። በዚህ ወቅት ሁለት ትላልቅ ተግባራትን እንዳስፈፀመ ይናገራል። አንደኛው በባህል ሚኒስቴሩ የሚተዳደሩ ተዋንያን፣ሙዚቀኞችና ተወዛዋዦች ቋሚ ደመወዝተኛ አልነበሩም የሚተዳደሩት በድጎማ ገንዘብ ነበርና ከትያትር ቤቶች ሥራ አስኪያጆች ጋር በመነጋገር ኮከብ፣ ምርጥና ምስጉን በሚሉ ደረጃዎች አመጣጥኖ ወደ ቋሚ ተከፋይነት እንዲያድጉ አድርጓል።
ሁለተኛው የመላው ዓለም ጥቁር ሕዝቦችና የአፍሪካውያን የባህልና የኪነ ጥበብ ክብረ በዓልን ኢትዮጲያ ኮከብ አዘጋጅ ሆና እንድታዘጋጅ ተመደበች፡፡ አያልነህም የተውኔቱን ቡድን እንዲመራ ታዘዘ። በአፍሪካ የሚነገሩ ቋንቋዎች ከመብዛታቸው የተነሳ ምን አይነት ተውኔት ብናቀርብ ሁሉንም ታዳሚያን በእኩል ማዝናናት ይቻላል የሚለው ጭንቀት ውዝግብ እንደፈጠረ አያልነህ ያስታውሳል። ይህንን ጥያቄ ለመመለስ "ቃል አልባ ተውኔት ይሁን" የሚል ሀሳብን አቅርቦ “ትግላችን” በሚል ርዕስ የሁለት ሰዓት (ማይም) ተውኔትን በመድረክ ላይ ለእይታ እንዲበቃ አደረገ። ስለ ተውኔቱ ይዘት ብቻ ሳይሆን ስለፈጠራው በተለያዩ ጋዜጦች ተሞገሰ።
"ትግላችን"
የኢትዮጲያ
ብቻ ሳይሆን የአፍሪካ ትግል ጭምር ነውም ተብሎ ተፃፈ። ስራውም በአገሪቱ ለቃል አልባ ተውኔቶች ፈር ቀዳጅ ሆነ። ክብረ በዓሉ እንዳበቃም የነአያልነህ ቡድን ናይጀሪያ እንዲቆይ ተደርጎ በበርካታ የትምህርት ተቋማት ትርኢቱ እንዲታይ ተደረገ።
ወቅቱ የአብዮት እሳት ግለቱ የጨመረበት ነበር። በዚህ ወቅት አያልነህ በሳንሱር ምክንያት ታሰረ። ከዚህ በኋላ ግን ባህል ሚኒስቴርን ለቆ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በመምህርነት ገባ። መምህርነቱን እንደቀጠለ
"የሥነ-
ፅሁፍ
ቅኝት"
እና ሌሎች የትያትር ማስተማሪያ መፀሃፍትን አዘጋጀ። ቀጥሎም በርካታ የጥበብ ሰዎችን አሰባስቦ የዩኒቨርሲቲውን
ባህል
ማዕከል
አቋቋመ።
በኋላም
የሚወደው
ሙያ ውስጥ እያለ ወቅቱ ኢ.ሠ.ፓ.አ.ኮ የሚቋቋምበት ነበርና በሥራ አስፈላጊነት ብለው እንዲቀላቀል ታዘዘ። ወዶ ሳይሆን በፍራቻ አራት ኪሎ ማዕከላዊ ኮሚቴ ፅህፈት ቤት ገባ። የፖለቲካ ተሿሚ ሆኖ እንኳ ልቡ የሚሳበው ወደ ኪነ ጥበቡ ነበር። በዘመነ ኢህአዴግ እንደገና ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተመልሶ ማስተማር ጀመረ። ይሁን እንጂ ከፈተና አትላቀቅ የተባለው ይህ ሰው በሚወደው ሞያ ውስጥ መቆየት አልቻለም። ከዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ ጋር መስማማት አልቻልክም በሚል ምክንያት ከዩኒቨርሲቲው ተባረረ። በባህል ማዕከሉ ውስጥ አብረውት የሚሰሩ ወደ 20 የሚደርሱ ወጣቶችንም አብረው ተባረው ነበርና የነዚህ ልጆች መባረር ምክንያት ነኝ ብሎ በማሰቡ ለነዚህ ወጣቶች መጠነኛ ገቢ የሚያገኙበትን ቀንዲል ቤተ ተውኔትን ማቋቋም ችሎ በርካታ ተንኳሽ ይዘት ያላቸው ተውኔቶችን ለእይታ ማብቃት ጀመረ። እነዚህን ተውኔቶች ለመድረክ ሲያበቃ ግን የተጋፈጣቸው ፈተናዎች ቀላል አልነበሩም።
አያልነህ እነዚህን በርካታ የብዕር ቱርፋቶች እያበረከተ በተጎዳኝ 1966-2004 ባለው ግዜ ውስጥ ከፍተኛ የሩሲያ ቋንቋ ጥናት ትምህርት ተከታትሎ ከሞስኮ የፑሸኪን ተቋም ከፍተኛ ዲፕሎማ አግኝቶል። አሁን ላይ ይቅርታ ተጠይቆ ወደሚወደው ሞያ ተመልሶ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህርነቱን ቀጥሏል ።
የትምህርት ደረጃ
• የዶክትሬት ድግሪ (1982)
የዶክትሬት ዲግሪ ማሟያ የጽሑፍ ሥራው (518-ገጽ) ሙሉ-በሙሉ ተጠናቆ ሞስኮ ለመንግሥት ዩኒቨርሰቲ የፈተና ቦርድ ቀርቦ የፀደቀ፣ ተጨማሪ የጽሑፍና የቃል ፈተናዎች እጅግ በጣም ጥሩ (Excellent) የሚል ውጤት ያገኙ፣ (በወቅቱ በነበረው ሁኔታ ሞስኮ ሄዶ ድግሪውን ለመቀበል አልተቻለም)
• የማስተርስ ዲግሪ
በሥነጽሁፍና ጋዜጠኛነት ሙያ በሞስኮ የመንግሥት ዩኒቨርስቲ ሁለተኛ ድግሪ (1967 )
• በልዩ የመምህራን ስልጠና ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በበዕደማርያም መለማማጃ ት/ቤት ልዩ ዲፕሎማ (1958 )
• ከፍተኛ የቋንቋ ዲፕሎማ ከሞስኮ የፑሽኪን ተቋም በሩሲያ ቋንቋ ከፍተኛ ዲፕሎማ ፣ (1996/2004)
የስራ ልምድ
1. የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር ም/ፕሬዚደንት (2005-10)
2. የኪነጠቢባን በጎ አድራጎት ማህበር ፕሬዚደንት (ከ2003-2016)
3. የሩሲያ ሳይንስና ባህል ማዕከል ም/ ዳይሬክተር (ከ1991-2001)
4. መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የሥነምግባር ኮሜቴ ዳይሬክተር (ከ2006-2015)
5. የዩኒቲ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ ባህል ማዕከል ዳይሬክተር (ከ1994-1996)
6. የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የባህል ማዕከል የቦርድ አባል (1996)
7. በኢትዮጵያ የመጀመሪያው የግል ቲያትር ቤት (ቀንዲል ቤተ ተውኔት) መሥራችና ዳይሬክተር ከ1985 ጀምሮ፣
8. ጉብል የህጻናት ጋዜጣ አዘጋጅና መሥራች (1987-2000)
9. በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህር፣ የባህል ማዕከሉ መሥራችና ዳይሬክተር (1971-72)
10. በኢሠፓ የስፖርትና የባህል መምሪያ ም/ ኃላፊ
(1972-1983)
11. የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የባህል ማዕከል ዳይሬክተር (1985)
12. በባህልና ስፖርት ሚኒስቴር የቲያትር ጥበባት ድርጅት ተጠሪ (1968-1971)
13. በኮተቤ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት የአማርኛ ቋንቋና ስነ-ጽሁፍ መምህር (1961-1963)
14. በሬዲዮ ሞስኮ የአማርኛ ክፍለ ጊዜ ‹‹የገጣሚው ደብተር›› በሚል ርዕስ በሳምንት ሁለት ጊዜ የሥነጽሑፍ ፕሮግራም አቅራቢ (1964-1967)
15. ከፍተኛ ተርጓሚ በፕሮግረስ አሳታሚ ድርጅት(1965-1967)
የብዕር ትሩፋት
I. ለመድረክና ለሕትመት የበቁ የሙሉ ጊዜ ተውኔቶች፤(Priting Full Length Plays)
1. እሳት ሲነድ በ1968-በመዘጋጃ ቤት፣ (በ2012 በመድበለ ተውኔት ቅጽ-አንድ የታተመ)
2. ሻጥር በእየፈርጁ በ1970-በብሔራዊ ቴያትር፣ (በ2012 በመድበለ ተውኔት ቅጽ-አንድ የታተመ)
3. የገጠሯ ፋና በ1970-በሀገር ፍቅር ቲያትር፣ (በ2012 በመድበለ ተውኔት ቅጽ-አንድ የታተመ)
4. የፊት እድፍ በ1972 በሀገር ፍቀር ቴያትር፣ (በ2012 የታተመ)
5. ጥልቅ ዐይን በ1977 በራስ ቲያትር፤(በ2012 የታተመ)
6. የመንታ እናት በ1972 በብሔራዊ ቲያትር፤(በ2012 በመድበለ ተውኔት ቅጽ-አንድ የታተመ)
(ለአገሪቱ መሪ በመክፈቻው ቀን ብቻ ቀርቦ የተዘጋ
7. ዱባና ቅል በ1972 በሀገር ፍቅር ቲያትር፣(በ2012 በመድበለ ተውኔት ቅጽ-አንድ የታተመ)
8. እጄን በእጄ በ1998 በቀንዲል ቤተተውኔት፣((በ2012 በመድበለ ተውኔት ቅጽ-አንድ የታተመ)
9. ሰባራ ዘንግ በ1999 በቀንዲል ቤተተውኔት፣(በ2012 በመድበለ ተውኔት ቅጽ-አንድ የታተመ)
10. ከድጃ በ1995 በቀንዲል ቤተተውኔትና በአገር ፍቅር፤(በ2012 በመድበለ ተውኔት ቅጽ-አንድ የታተመ)
11. ጥበበኛዋ ጋለሞታ.. ትርጉም፤በጣሊያንና በሩሲያ የባህል ማዕከላት መድረኮች የቀረበ፣ (በ1986-የታተመ)
12. ድሃ አደግ.. በለንደንና በአዴንብራ መድረኮች የቀረበ፣ በአማርኛና በእንግሊዝኛ በ1986 እና በ2000 የታተመ፣
13. ሾተላይ.. በሩሲያ የባህል መድረክ የቀረበ.. በ1991 የታተመ፤
14. ደረጃ.. ሙዚቃዊ ድራማ..፣ በሩሲያ የባህል ማዕከል መድረክ የቀረበ..፣ በ1986 የታተመ፤
15. ፊሉሜና ማራቱራና… በዲ. ፊሊፖ ተጽፎ ተተርጉሞ በ2001 የታተመ፤ በ2013 በብሔራዊ ቴያትር የቀረበ፤
16. የደም ጋብቻ የጋርሲያ ሎርካ ሥራ ትርጉም፣ በብሔራዊ ቲያትር ለሚኒስትሮችና አምባሳደሮች አንዴ ብቻ የታዬ፣ በ2000 የታተመ፣(የኢትዮጵያ ሕዝብ ያላየው)
17. የመንታ እናት በ1972 በብሔራዊ ቴያትር የቀረበ፤(ለአገሪቱ መሪ በመክፈቻው ቀን ብቻ ቀርቦ የተዘጋ)‹‹በምርጥ የአፍሪካ ጸሀፊ ተውኔቶች መድበል›› ላይ በ1975 በሞስኮ በሩድጋ አሳታሚ ድርጅት በሩሲያ ቋንቋ ተተረጉሞ የታተመ፣
2.ያልታተሙ የሙሉ ጊዜ ተውኔቶች(Unpublished Full Length Plays)
18. በጋሜ መቅረት በ1995 በቀንዲል ቤተተውኔት የቀረበ፤ (በተውኔት-ጉባዔ ቅጽ-ሁለት የተካተተ)
19. ጎልጃና ታምራት በ1975 ጦር ግንባር የተፃፈ፤(በተውኔት-ጉባዔ ቅጽ-ሁለት የተካተተ)
20. ማምሸትም ዕድሜ ነው በ1977 በወሎ ድርቅ ላይ የተፃፈ ቅጽ-ሁለት የተካተተ)
2. የከበረ ድንጋይ በ1976 የተፃፈ መድረክ ያጣ፤ (በተውኔት-ጉባዔ ቅጽ-ሁለት የተካተተ)
3. አባቦራ በ2012 ለመድረክ ተዘጋጅቶ ማሳያ ቦታ ያጣ (ስለገረሱ ዱኬ)
4. የአገው ትውፊታዊ ተውኔት በብሔራዊ ቴያትር ጥያቄ መሠረት ተዘጋጅቶ ያልተተገበረ፤
21. እምቢበል በ1984 የተፃፈ (በተውኔት-ጉባዔ ቅጽ-ሁለት የተካተተ)
5. ዶክተር አበባው በ1985 የተፀፈ መድረክ ያጣ(በተውኔት-ጉባዔ ቅጽ-ሁለት የተካተተ)
6. የጦር ሜዳው ገድል በ1974 በነቅፋና ባፋቤት ቆይታዬ የፃፍሁት፤በተውኔት-ጉባዔ ቅጽ-ሁለት የተካተተ)
7. በላይ ዘለቀ በ2007 ለፊልምና ለመድረክ የተፀፈ፤
8. ጉቶ በ1980 የተፃፈ(በተውኔት-ጉባዔ ቅጽ-ሁለት የተካተተ)
9. አስተማሪዋ ሉባ በ2003 መድረክ ያጣ፣ (ትርጉም-ሲሞኖቭ)፣
10. የገጣሚው ዕጣ ፈንታ በ1994 በቀንዲል ቤተተውኔት፣ ተዘጋጅቶ መድረክ አጥቶ የቀረ፤(በተውኔት-ጉባዔ ቅጽ-ሁለት የተካተተ)
11. ለተብርሃን በ1999 በቀንዲል.. በሀገርፍቅር..በሜጋ፣
12. የጊዜው ተቆጣጣሪ በ1998 በቀንዲል.. በሀገርፍቅር፣ በሜጋ፣ የቀረበ፣ (ትርጉም-የጎገል)
13. ዶክተር ጋጋኖ በ1996 በቀንዲል የቀረበ፣ (ትርጉም-የቸሆቭ)
14. የእንጆሪ ማሳ በ2004 በኢምባሲ መድረክ የቀረበ፣ (ትርጉም-የቸሆቭ)፣
3.የታተሙ ግጥሞች፤(Printing poems)
15. ትግላችን.. የግጥም ስብስብ፣ በ1967 በአውሮፓ የኢትዮጵያ ተማሪዎች የታተመ፣
16. 35 የግጥሞች ስብስብ.. በ1968 በኢትዮጵያ ተማሪዎች ፌዴሬሽን ልዩ እትም
17. ጽጌረዳ ብዕር.. በ1978 በጋራ መድብል ላይ የታተሙ ሆነ፤የተለያዩ ግጥሞች ፤
18. ማን ይሆን የበላ? የግጥም ስብስብ በ1984 የታተመ፣
19. ጥገት ላም.. የግጥም ስብስብ በ1985 የታተመ፣
20. ፑሽኪን.. ግለ-ታሪኩና የተመረጡ ግጥሞች ስብስብ፣ በ1991 የታተመ፣
21. 60 የተለያዩ ግጥሞች... በዓለምና በሀገር አቀፍ ጋዜጦች ላይ ከ1963-1968
የታተሙ፣
22. 595 የተለያዩ ግጥሞች በሬዲዮ ሞስኮ የአማርኛ ፕሮግራም ላይ ከ1964-1968 የቀረቡ፣
23. ወይ አንቺ አገር... የግጥም ስብስብ በ2004 የታተመ፣(1200
ገጽ)
24. ከድጡ ወደ ማጡ... የግጥም ስብስብ በ2004 የታተመ፣
(1200 ገጽ)
25. የአፍሪካ ባህል ቅኝት.. በአፍሪካ-ኤስያ መጽሔት ላይ የታተመ ጥናት፣(1966
እ.ኢ.አ.)
26. የሥነ-ጽሑፍ ቅኝት.. በ1977 የታተመ፣ በዩኒቨርሰቲ ረ/ማስተማሪያ (360 ገጽ)
II. ከአማርኛ ወደ ውጭ ቋንቋ የተተረጎሙ የደራሲው ሥራዎች፤(Translated poems from Amharic to Russia)
27. የተለያዩ ግጥሞች... ‹‹ምርጥ የአፍሪካ ገጣሚያን ስራዎች›› በሚል ርዕስ፣ በ1971 በሩሲያ ቋንቋ ተተርጉመው የታተሙ፣
28. መስቀል አበባ... በሚል ርዕስ በ1982 በሩዱጋ አሳታሚ ኤጀንሲ በሩሲያ ቋንቋ ተተረጎመው የታተሙ የተለያዩ ግጥሞች፣
29. አጭር የህይወት ታሪክ... በ1970 በታተመው በታላቁ የሶቬየት ኢንሳይክሎፒዲያ በቅጽ አንድ ገጽ 317 ላይ ሠፍሯል፣
III. ደራሲው ከውጭ ቋንቋ ወደ አማርኛ የተረጎማቸው ግጥሞች፣(Poems Translated from Russia to Amharic)
30. የፑሽኪን የተለያዩ ግጥሞች፤
31. የኒክራሶቭ... ኒኩላይ አሌክሲቪች ግጥሞች፣ /1813-1870/
32. የክሪሎቭ... ሰውኛ ግጥሞች፣
33. የሌርሞንቶቭ... ሚካኤል ቦንጎቪች ግጥሞች፣ /1804-1833/
34. ከማያኮቭስኪ... ቭላድሚር ቫላዲሚሮቪች ግጥሞች፣ /1885-1922/
35. የኢሰኒን... ሰርጌ አሌክሳንድሮቪች፣ ግጥሞች፣ /1888-1918/
36. የማክሲም ጎርኪ...አጫጫር ታሪኮች.. ሁሉም በሞስኮ ሪዲዎ ‹‹በገጣሚው ደብተር›› ፕሮግራም ላይ ቀርበዋል፣
(1963-67)
37. ራስል ጋምዛቶቭ...የዩክራይን ገጣሚ ብሄራዊ መዝሙር ወደ አማርኛ ተተርጎሞ በ1983 በዩክሬን ታትሟል፡፡
38. የፓን አፍሪካ ደራሲያን... የሲዛር ኤሜ፣ የጎዩሊን.. የተለያዩ በርካታ ግጥሞች ተተርጉመው በ1977 የታተሙ፣
IV. ለሕትመት ያልበቁ ሥራዎች፤ (Unpublished works)
39. የዓለም ሥነ-ጽሑፍ ቅኝት.. 1977 የታተመ፣ በዩኒቨርሰቲ ማስተማሪያ የሚሆን (360 ገጽ)
40. የዲሞክራሲያዊ ባህል ግንባታ.. በ1978 የተዘጋጄ፣ (400 ገጽ)
41. የኢትዮጵያ ሥነ-ጽሑፍ ቅኝት.. በ1981(እ.ኢ.አ.) ሞስኮ የመንግሥት ዩኒቨርስቲ ለዶክትሬት ዲግሪ ማሟያ ቀርቦ የፀደቀ (518ገጽ) በእንግሊዝኛ ቋንቋ የተዘጋጄ)
42. የሥነጽሑፍ መዝገበ ቃላት.. በ1991 የተዘጋጀ፣ (525 ገጽ)
43. ጸሀፊ-ተውኔት፣ አዘጋጅና ተዋናይ... በ1990 የተዘጋጄ የቲያትር ማስተማሪያ (620 ገጽ)
44. የአፍሪካ ተረቶች... በ1992 የተጠናቀረ (ያልታተመ 560 ገጽ)
45. የሥነጽሁፍ ቅኝት... ቅጽ ሁለት በ1990 የተዘጋጄ (ያልታተመ 875 ገጽ
V. በመድረክ /በቲቨ/ በሬዲዎ የቀረቡ ባላንድ ገቢር ተውኔቶች (One Act plays)
46. አንድ-ለአንድ በ1978 በብሔራዊ ቲያትር፣ (ለሴቶች ቀን ብቻ ለኃላፊዎች ቀርቦ የተዘጋ)
47. ቡና እንደ በርበሬ በ1975 በሐገር ፍቅር፣ በጎንደር ኪነት፤
48. በቡ ድል ሲመታ 1971 በሀገር ፍቅርና በክ/ሀገራት
49. ነግ በእኔ 1972 በጎንደር ኪነት፤
50. ዳቦ አይሆን ከተማ በ1971 በከነማ መድረኮች የቀረበ፤
51. ትራፊክ (ቁራ) በ1971 በቴሌቪዥን በወጋየሁ የቀረበ፤
52. እኔና እሱ በ1972 በአኢሴማ አዳራሽ ላንዴ ብቻ የታዬ፤
53. የዘመቻው ጥሪ በ970 ስለብሔራዊ ውትድርና የተዘጋጀ፤ (በቀበሌዎች መድረኮችና በቲቪ የቀረበ፣
54. ቢሮክራትና ተረቱ በ1971 በአዲስ አበበባ ዩኒቨርስቲ በህል ማዕከል፣
55. ብናኝ አፈር ከሐገሬ.. በ1974 ምጽዋ (ለቀይ ኮከብ ዘመቻ ምጽዋ ባህሩ ዳር የቀረበ)
4.ሙዚቃዊ ድራማዎች (Musical Plays)
56. ትግላችን... ማይም ወይም ድምጽ አልባ ድራማ.. በጥቁር አፍሪካውያን የባህል ፌስቲቫል ላይ ናይጄሪያ-ሌጎስ በ1969..፣ ሃቫና ኩባ በወጣቶች ፌስቲቫል በ1970 የቀረበ፣ (ከጉዞ ሲመለስ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ያላየው)
57. ህዝብ-lህዝብ (አደይ አበባ) በአውሮፓ.. በአሜሪካ.. በካናዳ.. በላቲን አሜሪካ.. በሶቪየት ሕብረት በ1980 የታዬ፡፡(ከጉዞ ሲመለስ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ያላየው)
58. ሉሲ ሙዚቃዊ ድራማ.. በ2001 በአልጀርስ የፓን አፍሪካ ፌስቲቫል ላይ የቀረበ ነው፣(ከጉዞ ሲመለስ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ያላየው)
59. አንድነት በዘመናዊ ሙዚቃና ዳንስ የተቀነባረ ማይም ድራማ፣ በ1972 በብሄራዊ ትያትር ለአንዴ የታየ፣(ለአገሪቱ መሪ በመክፈቻው ቀን ብቻ ቀርቦ የተዘጋ)
60. መስከረም በባህላዊ ሙዚቃና ውዝዋዜ የተቀነባበረ ማይም ድራማ.. በ1972 በሀገር ፍቅር ትያትር የታየ፣ (ለአገሪቱ ም/መሪ በመክፈቻው ቀን ብቻ ቀርቦ የተዘጋ)
61. ጉዞአችን በዘመናዊ ሙዚቃና ዳንስ የተጋጄ ማይም ድራማ.. በ1975 በብሄራዊ ትያትር የቀረበ፣ (ለአገሪቱ መሪ በመክፈቻው ቀን ብቻ ቀርቦ የተዘጋ)
62. ኅብረ-ዝማሬ በዘመናዊ ሙዚቃና ዳንስ የተጠናቀረ ማይም ድራማ..፤በ1978 በኮንግረስ አዳራሽ የታዬ፣ (ለአገሪቱ መሪ በመክፈቻው ቀን ብቻ ቀርቦ የተዘጋ)
69 ስደት-ለምኔ በዓለም የስደተኞች ቀን 50ኛ ዐመት በዓል በ1992 በአውሮፓ ህብረት የስብሰባ አዳራሽ የቀረበ፣ ማይም ድራማ፣(የኢትዮጵያ ሕዝብ ያላየው)
70 ደረጃ በቀንዲል ቤተተውኔት በ1986 የቀረበ ሙዚቃዊ ድራማ፤
71 የፆም ቋንጣ በራስ ቴአትር በ1993 የቀረበ ሙዚቃዊ ድራማ፣
72 የህይወት መድኅን በመጀመሪያው የዓለም ኤች አይ ቪ ኤድስ ጉባኤ ላይ በአፍሪካ አንድነት አዳራሽ በ1993 የቀረበ ማይም ድራማ፣
73 ጆፌ አሞራ በዩኒቲ ዩኒቨርስቲ በ1992 የተዘጋጄ ማይም ደራማ፤
74 የፍቅር መድሃኒት በ1999 በቀንዲል ቤተተውኔት በበህላዊ ሙዚቃና ውዘዋዜና የተዘጋጄ ማይም ድራማ፣
75 አዲስ አራዳ በ2001 በማዘጋጃ ቤት የቀረበ ሙዚቃዊ ድራማ፣
76 አባይ አግሳ 2004 ለሕዳሴው ግድብ ጽ/ቤት ተውኔቱ የቀረበ፤
77 ከ25 በላይ የፈጠራ ስራዎችና ትርጉሞች ከመንግሥትና ከግል ተቋማት ጋር በመተባበር በተለያዩ ፕሮግራሞችና ሚዲያዎች ለህዝብ ቀርበዋል፡፡
78 በርካታየሕፃናት ድራማዎች በሬዲዮ፣ በቴሌቪዥን፣ በቀንዲል መድረኮች ቀርበዋል፡፡
79 ፊልሞች አነጋጋሪና በሣል ያወቂ ፊልሞችም በቴሌቪዥን ታይተዋል፣ በሬዴዎ ተደምጠዋል፡፡
(ያይኔ..፣ የሕዝብ ዐይኖች..፣ ሰንተል..፣ ያለዕድሜ ጋብቻ.. ትንኮሳ..፣ ትዳር-ለምኔ፣ ሰንተል፤ ሶነን ፣ ትንኮሳ ወዘተ..)
መዝጊያ፤ ጸሀፌ-ተውኔት እና የኪነጥበብ ሰው አቶ አያልነህ ሙላቱ ባለፉት 50 አመታት በሀገራችን የስነ-ጽሁፍ እና የቴአትር፤ የሙዚቃ እንቅስቃሴ ውስጥ እንደ ዋና ባለውለታ ሆኖ ሳይታክት የታገለ ባለሙያ ነው፡፡ ጋሽ አያልነህ ሙላቱ ህይወቱን ያሳለፈው ከጽሁፍ ስራ ጋር ነው፡፡ ድራማዎችን ይደርሳል፡፡ ሙዚቃዊ ተውኔቶች መድረክ ላይ እንዲቀርቡ ያደርጋል፡፡ ከስነ-ጽሁፍ ጋር የተያያዙ የጥናትና የምርምር ስራዎችን ያሳትማል፡፡ ግጥም ይጽፋል፡፡ ጋሽ አያልነህ ለህትመት ያልበቁ ስራዎችን ጨምሮ ከ80 በላይ የጥበብ ስራዎች እውን ያደረገ ነው፡፡ ኢትዮጵያ አሁን ካሏት የጥበብ ሰዎች በግንባር ቀደምትነት ከሚጠቀሱት አንዱ ነው፡፡ በአንጋፋነት ብቻ ሳይሆን ብዙ ስራዎችን በመስራት ሀገሩ የምትጠብቅበትን ትልቅ ሀላፊነት የተወጣ ነው፡፡ ምናልባትም ጋሽ አያልነህ ለታላላቆቹ ሎሬቶች ጋር ስሙ የሚጠራ ፤ ስራዎችን በጥራት የሚሰራ ብሎም ደግሞ ወጣት የጥበብ ባለሙያዎች በሙያው እንዲያድጉ የበኩሉን የተወጣ ታላቅ የኪነ-ጥበብ አርበኛ ነው፡፡ የዚህ ዊኪፒዲያ አዘጋጆች የጸሀፌ-ተውኔት አያልነህ ግለ-ታሪክ አሁን በተጻፈው መልኩ እንዲሰነድ ስንወስን ያለፈበት መንገድ ብዙዎችን የሚያስተምር ነው፡፡ ጋሽ አያልነህ ዛሬም ለመጻፍ አልተቆጠበም፡፡
ያነባል፤
ይመራመራል፤
የተለያዩ
መድረኮች
ላይ ይታደማል፡፡ ኢትዮጵያ የጋሽ አያልነህን ውለታ ከቶ ልትዘነጋው አትችልም፡፡ የሰራው ራሱን ደስ ለማሰኘት ብቻ ሳይሆን ሀገሩ በኪነ-ጥበብ አንድ ሰው እንዳላት ለማሳየት ነው፡፡ ጋሽ አያልነህ ሀገሩን ይወዳል፡፡ ከመውደድ ባለፈ ደግሞ ዋጋ ለመክፈል የቆረጠ ነው፡፡ ለሀገር የሰሩ ሰዎች ታሪካቸው በግለ-ታሪክ መልክ / አሁን በተሰራው መልክ/ መሰነድ ባልተለመደበት ሀገር የጋሽ አያልነህ ይህ ግለ-ታሪክ ብዙ የሚያስተምር ነው፡፡ ጋሽ አያልነህ ከዚህ በላይ ለሀገሩ ለማበርከት ይፈልጋል፡፡ የሰራቸው ስራዎች ለአዲሱ ትውልድ እንዲሸጋገሩም ይፈልጋል፡፡ እኛ የዚህ ዊኪፒዲያ አዘጋጆች ጋሽ አያልነህን ከ 20 አመት ጀምሮ በቅርበት እንደማወቃችን ምን ያህል ለስራው ቅድሚያ የሚሰጥ ሰው እንደሆነ መመስከር እንችላለን፡፡ ሁሉም ጋሽ አያልነህ ብቁ ያደረጋቸው የኪነት ሰዎችም በሙሉ አንደበታቸው እንደሚመሰክሩት ታላቁ ሰው ጋሽ አያልነህ ለብዙዎች ውለታ የዋለ ነው፡፡ ለዚህ ውለታው እውቅና ማግኘት እንዳለበት ብዙዎች ይስማማሉ፡፡ እናም እኛ የምንለው ጋሽ አያልነህ እናከብርሀለን፤ እንወድሀለን ነው፡፡ ህዳር 12 ደግሞ የተወለድክባት ቀን ስለሆነች 1 ወር ቢቀረውም እንኳን አደረሰህ ማለት እንወዳለን፡፡ / የዚህ ጽሁፍ የምርምር ፤ የጽሁፍ እና የማዋቀር ስራ ሙሉ በሙሉ በዘቢባ ሁሴን የተሰራ ሲሆን የአርትኦትና የመዝጊያ የአቋም መግለጫ ጽሁፍ ደግሞ በጋዜጠኛ እዝራ እጅጉ የተሰራ ነው፡፡ ይህ ጽሁፍ ዛሬ ጥቅምት 4 2014 በተወዳጅ ሚድያ የፌስ ቡክ ገጽና በዊኪፒዲያ ገጽ ላይ ወጣ፡፡
አስተያየቶች
አስተያየት ይለጥፉ