106. መላኩ ብርሃኑ ተስፋዬ-MELAKU BERHANU TESFAYE
ታታሪውና ሁለ-ገቡ መላኩ ብርሀኑ
የዚህ ታሪክ
አሰባሳቢ፣ ተወዳጅ ሚድያና ኮሚኒኬሽን በስነ-ጽሁፍ፣
በስነ-ስእል፣ በፊልም ፣ በቴአትር፣ በሬድዮ ድራማ ፤ በማስታወቂያ ዘርፍ ፤ በሚድያ ዘርፍ ከ1990ዎቹ ጀምሮ አስተዋጽኦ
ያበረከቱና አሁንም በስራ ላይ ያሉ ባለሙያዎችን ታሪክ በፌስ ቡክ ፤ በዊኪፒዲያ እንዲሁም በሌሎች የማህበራዊ ሚድያዎች
እያስተዋወቀ እንዳለ ይታወቃል፡፡ ውድ ይህን ሀሳብ የምትደግፉ
መስፈርቱን ያሟላሉ የምትሏቸው ሰዎች ጠቁሙን ፤ እርስዎም ታሪኬ መሰነድ አለበት ካሉ ይላኩልን፡፡ ከተቀመጠው መስፈርት
አንጻር አይተን ታሪክዎን እናወጣለን፡፡ በ tewedajemedia@gmail.com ግለ-ታሪክዎን ይላኩ፡፡ ጥቅምት 14 2014
የ1000 ሰዎች ታሪክ ሲሞላ ድንቅ ታሪካዊ ምረቃ ይኖራል፡፡ ታሪካቸው አሁን የሚሰራላቸው፤ ብዙዎቹ በወጣትነት አንዳንዶቹም
በጉልምስና እድሜ ላይ የሚገኙ ሲሆኑ የዛሬ ጎልማሳ የነገ የሀገር ባለውለታ ነውና ታሪካቸውን እየሰነድን ለትውልድ
እናስቀምጣለን፡፡ ለወደፊቱም ምርምር ለሚያደርጉ እና ወይም የስራ ፕሮጀክቶቻቸውን ለሚደግፉ ሰዎች ይጠቅማል ብለን እናምናለን፡፡
በ7 ዘርፎች ትልቅ ስራ ሰርተዋል ብለን ያመንባቸውን ሰዎች ታሪክ እናቀርባለን፡፡ ይህ የማስተዋወቅ ስራ ውድድር ሳይሆን በሙያው
የተለየ ሚና ያበረከተ ማንኛውም ሰው ታሪኩ የሚሰነድበት ነው፡፡ ጋን በጠጠር ይደገፋል እንዲሉ ሙያቸውን በመደገፍ የራሳቸውን
አሻራ ያኖሩ ሰዎች ታሪካቸው ይዘከራል፡፡ አሁን ከሚድያ ዘርፍ
ታሪኩ የሚቀርብለት ሰወ ታታሪውና ሁለ-ገቡ መላኩ ብርሀኑ ይሆናል፡፡
ትውልድ ፤ልጅነት
ጋዜጠኛ መላኩ
ብርሀኑ አዲስ አበባ ከተማ በተለምዶ ‹‹ኦሎምፒያ›› ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ተወለደ። በትንሳዔ ብርሃን እና በቦሌ ከፍተኛ
ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ውስጥ የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ተከታትሏል። ከተማሪነት ዘመኑ ጀምሮ ላደላበት
የስነ-ጽሁፍ ፍቅር የተሸነፈው በጊዜ ነው። ሲመኘው የኖረውን ጋዜጠኛ የመሆን ህልም ለማሳካት መንደርደሪያዎቹ የተማረባቸው
ትምህርት ቤቶች ሚኒ ሚዲያዎች ነበሩ። ለዚህ ደግሞ የመጀመሪያ ልብ-ወለድ ስራውን አይተው ወደሚኒ ሚዲያ እንዲመጣ ብርታት
የሰጡትን የ9ኛ ክፍል የአማርኛ መምህሩን አቶ አለማየሁ የስጋትን ያመሰግናል።
የንባብ ፍቅር-የመጻፍ ክህሎት
መላኩ፤ ጋዜጠኝነትን
ከመስራቱ አስቀድሞ ረጅም አመታትን በንባብ አሳልፏል። የአባቱን የንባብ ፍቅር እያየ ያደገ በመሆኑም ከእድሜው የቀደሙ
መጽሃፍትን በልጅነቱ ለማንበብ እድል አግኝቷል። ‹‹ጣምራ ጦር›› የሚለውን የገበየሁ አየለ መጽሃፍ የ3ኛ ክፍል ተማሪ ሆኖ
ማንበቡን ይናገራል። ከዚያ በኋላም ‹‹ስደተኛው››፣ ‹‹ደራሲው››፣ ‹‹የቀይ ኮከብ ጥሪ››፣ ‹‹ብቀላ›› እና የመሳሰሉ ዳጎስ
ያሉ መጽሃፍትን በልጅነቱ አንብቧቸዋል። ይህ የማንበብ ፍቅሩ እጁን ማፍታታት እስከጀመረበት እስከ 9ኛ ክፍል ድረስ ከዚያም
ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን እስኪጨርስ ድረስ አብሮት ኖሯል። “በዘመኑ የታተሙ ፣ እኔ ያላነበብኳቸው መጽሃፍት የሉም” ይላል
በሙሉ ልብ። መጽሃፍቱ የዛሬ ማንነቱንና አስተሳሰቡን የቀረጹለት በመሆናቸውም አሁን ድረስ በልጅነቱ ማንበብ መጀመሩን እንደአንድ
የህይወቱ አዲስ የተከፈተ መጋረጃ ይቆጥረዋል።
“ለእኩዮችህ አርአያ
ሆነህ ማደግ አለብህ” የሚሉትንና የሚወዳቸውን እናቱን ቃል እየሰማ ማደጉን የሚናገረው መላኩ ያንን ቃል ለማክበርና ቤተሰቦቹ
በሚፈልጉት ቦታ ለመገኘት ህይወቱን በስርዓት አስገዝቶ በልጅነት እና ወጣትነት ሳይታለል ያሰበበት ለመድረስ ጉዞ የጀመረውም
በልጅነቱ መሆኑን ይናገራል።
አባቱ ለስራ ጉዳይ
በኢትዮጵያ የተለያዩ ክፍላተ ሃገራት ይዞሩ ስለነበር የመጻፍ ችሎታውን ያሟሸው ለርሳቸው የሰላምታ ደብዳቤ በመጻፍ መሆኑንና
የስነጽሁፍ ችሎታውን ያዩ ጎረቤቶቹና የአካባቢው ሰዎችም ለቀበሌ ማመልከቻ የሚያጽፉት እርሱን እንደነበር በፈገግታ ያስታውሳል።
መላኩ ለልጅነቱ ፣
ለትውልድ ሰፈሩ እና እና ላደገበት ማህበረሰብ ልዩ ፍቅርና ህይወቱን ሙሉ የማይዘነጋውን ናፍቆትና ትውስታ ሲገልጽ “ዘነበ ወላ
“ልጅነት” የሚለውን መጽሃፍ ቀድሞኝ ባይጽፍ ኖሮ የልጅነት ታሪኩን የሚጽፍ አንደኛ ደራሴ እኔ መሆኔ አይቀርም ነበር” በማለት
ነው። የአለማየሁ ገላጋይን “የብርሃን ፈለጎች እና የዘነበ ወላን ልጅነት የራሴ የልጅነት ዘመን ማስታወሻ አድርጌ ስለምቆጥራቸው
ከሁሉም መጽሃፍት የበለጠ ዋጋ እሰጣቸዋለሁ” ነው የሚለው መላኩ።
መላኩ መደበኛ
ትምህርቱን ከማጠናቀቁ አስቀድሞ በተለያዩ የስነጽሁፍ ውድድሮች እየተሳተፈ ችሎታውን ያዳብር ነበር። የስነጽሁፍ እና ግጥም
አስተዋጽዖ በሚፈለግበት ቦታ ሁሉ ስራዎቹን እያቀረበ ምስጋናም ይቸረው እንደነበር ይገልጻል።
የጋዜጠኝነት አለም
12ኛ ክፍልን
አጠናቅቆ ከመደበኛ ትምህርት ቤት ከወጣ በኋላ የመጀመሪያውን የጋዜጠኝነት ስልጠና ከፎቶግራፍ ሙያ ጋር አጣምሮ የወሰደው
በቀድሞው የኢትዮጵያ ፖሊስ ኮሌጅ በዛሬው የፖሊስ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ነው። በስልጠና ላይ እያለ “ኮርስ ሜቶቼ” የሚላቸው የርሱ ባቾች /እኩያ ባልደረቦች/የሚያውቁትና
ሁሌም የሚያስታውሱት በስነጽሁፍ ስራዎቹ ነው።
መላኩ ወደመደበኛ
የጋዜጠኝነት ስራ የገባው ከፖሊስ ኮሌጅ ምረቃ በኋላ ነው። ለመጀመሪያ ጊዜ የጋዜጠኝነት ሙያ አገልግሎቱን በወንጀል ዘገባ ዘርፍ
አሃዱ ብሎ ጀመረ። በጊዜው ለፖሊስና ርምጃው ጋዜጣ እንዲሁም ለፖሊስና ህብረተሰብ የራዲዮና ቴሌቪዠን ፕሮግራሞች 1989 ዓ.ም
የአዲስ አበባ ሪፖርተር ሆኖ መስራት ጀመረ።
በፖሊስ ሚዲያ ውስጥ
ትክክለኛውን የጋዜጠኝነት ዘርፍ እንዳውቀውና እንድተገብረው መሰረት የሆነኝ ሰው የፖሊስና እርምጃው ጋዜጣ አዘጋጅና ታዋቂ
የስነጽሁፍ ሰው የነበረው የመጀመሪያ አለቃዬ መቶ አለቃ ሃይሉ አበበ ነው ይላል። ከፖሊስና ህብረተሰብ ሚዲያ ሪፖርተርነቱ በተጨማሪ ዘወትር ማክሰኞና ሃሙስ
ምሽት ላይ በአዲስ አበባ መገናኛ ብዙሃን (የቀድሞው ኢቲቪ 2) ላይ የሚተላለፈውን “አዲስ ፖሊስ” የሚባል የቴሌቪዠን ፕሮግራም
ከቡድን አባሎቹ ጋር በማስጀመር በዋና አዘጋጅነት ሰርቷል።አዲስ ፖሊስ የተባለ መጽሄትም መስራችና አዘጋጅ ሆኖ ሰርቷል።
መማር-መማር
የቀድሞው ዩኒቲ
ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ የአሁኑ ዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ በሃገሪቱ የመጀመሪያ የሆነውን የጋዜጠኝነት እና ኮሙኒኬሽን ትምህርት ቤት በመክፈት
በዲፕሎማ መርሃግብር ጋዜጠኞችን ማሰልጠን ሲጀምር መላኩ ‘የነፍሴ
ጥሪ ነው’ የሚለውን የጋዜጠኝነት ሙያ ሳይንሱ በሚፈቅደው ትምህርት ለማገዝ ወደዚያው አቀና። የሶስት ዓመት የጋዜጠኝነት
ስልጠናውንም በ1997 ዓ.ም በማዕረግ ተመራቂነት አጠናቀቀ።
የዩኒቲን የትምህርት
ዘመን “የህይወት ዘመኔ የሙያ መሰረት” ብሎ ይጠራዋል። ከዛሬዎቹ የቪኦኤ ዘጋቢ ጽዮን ግርማ ጀምሮ የዛሬው ሪፖርተር ጋዜጣ ዋና
አዘጋጁ ታምሩ ጽጌ፣ የቀድሞው ጦቢያና ልሳነ ህዝብ መጽሄት አዘጋጁ ታዬ በላቸው እንዲሁም ሌሎች በርካታ የዘመኑ ታዋቂ የግል
ፕሬስ ጋዜጠኞች የዩኒቲ ኮሌጅ ባቾቹ/ በአንድ ዘመን አብረው/ የተማሩ ናቸው።
መላኩ ዩኒቲን
ከተሰናበተ በኋላ በዚያው ዓመት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነት እና ኮሙኒኬሽን ትምህርት ቤት ከፍቶ ጋዜጠኝነትን በዲግሪ
ፕሮግራም መስጠት በመጀመሩ ወደዚያው በማቅናት በብሮድካስት
ጆርናሊዝም ዘርፍ በቴሌቪዠን ጋዜጠኝነት የመጀመሪያ ዲግሪውን አግኝቷል። ሮዝ መስቲካ፣ መሰለ ገብረህይወት ፣ ታምሩ ጽጌ፣ የትነበርክ ታደለ፣ ጸዳለ ለማ፣ በፍቃዱ በሻህ፣ አንዱአለም
ሲሳይ እና ሌሎችም የእርሱ ባቾች ዛሬ ድረስ ጋዜጠኝነትን አክብረው ያስከበሩ መሆናቸውን ይመሰክራል።
ከዚህ ዩኒቨርሲቲ
ተመርቆ ከወጣ በኋላ መላኩ ሙያውን በሳይንሳዊ ዕውቀት ለማበልጸግ የነበረው ፍላጎት ከአንድ አመት በላይ ከትምርት ርቆ
እንዳይቆይና ትምህርቱን እዚህ ላይ እንዳያቆም አድርጎታል። ቀጣዩ የትምህርት ጉዞው ህንድ ሃገር በሚገኘው ሲኪም ማኒፓል
ዪኒቨርሲቲ ኦፍ ቴክኖሎጂካል ሳይንስስ ወደተባለ ዩኒቨርሲቲ ነበር።
በዚያም በጆርናሊዝም እና ኮሙኒኬሽን ዘርፍ በኮርፖሬት ኮሙኒኬሽን ልዩ ሙያ (specialization) የማስተርስ
ኦፍ አርትስ ኢንተርናሽናል ዲግሪውን ተቀብሏል። መላኩ ከኮሌጅና
ዩኒቨርሲቲ መደበኛ ትምህርቶቹ ባሻገር ከ21 በላይ አጫጭርና ረጃጅም የጋዜጠኝነት ስልጠናዎችን በሃገር ውስጥና በውጭ ሃገራት
ተከታትሎ ሰርተፍኬቶችን አገኝቷል።
ሙሉ የስራ ዘመኑን
በጋዜጠኝነት እና ኮሙኒኬሽን ስራዎች ላይ ያሳለፈው መላኩ
ከእድሜው እኩሌታ የላቀ ዘመኑን በተለያዩ መገናኛ
ብዙሃን ላይ አገልግሏል። ለ9 ዓመታት በፖሊስ መገናኛ ብዙሃን ውስጥ ከሪፖርተርነት እስከዋና አዘጋጅነት በደረሱ መደቦች ላይ
በፖሊስ ራዲዮ፣ጋዜጣና ቴሌቪዠን እንዲሁም በአዲስ ፖሊስ ቴሌቪዠን ፕሮግራም እና መጽሄት ላይ ነው የሰራው።
በተጨማሪም በአዲስ
ልሳን ጋዜጣ እና ቀድሞ ኢቲቪ 2 ይባል በነበረው የአ/አ መገናኛ ብዙሃን ቴሌቪዠን ፕሮግራም ላይ በአምድ ጽሁፍ አዘጋጅነትና
እና በወንጀል ዘገባዎች አቅራቢነት ሰርቷል።
የኢትዮጵያ ዜና
አገልግሎትን ከተቀላቀለ በኋላም ለ7 ዓመታት ያህል በዜና አገልግሎቱ ከዜና ኤዲተርነት እስከ ፕሮግራም ፕሮዳክሽን ሃላፊነት
በደረሱ የጋዜጠኝነት ሙያ መደቦች ላይ እስከ 2004 ዓ.ም ድረስ አገልግሏል። “ጋዜጠኝነትን ሳስብ ለዜና አገልግሎት ቆይታዬ
ልዩ ከበሬታ እና ፍቅር አለኝ” ይላል።
መላኩ እና መምህርነት
መላኩ ከጋዜጠኝነት
ስራው ባሻገር መምህር በመሆንም እውቀቱን አካፍሏል። ለአዲስ አበባ ፖሊስ ማሰልጠኛ ማዕከል ሰልጣኞችም የህዝብ ግንኙነት
ትምህርት መምህር ሆኖ አገልግሏል። ከጋዜጠኝነት ስራው ጎን ለጎን እንደኢስት አፍሪካ ጆርናሊዝም አሊያንስ፣ ግሎባል ሄልዝ፣
ሲአርዲኤ፣ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤትና የመሳሰሉ ዓለምአቀፍና አህጉራዊ ተቋማት እንዲሁም የሃገር ውስጥ ድርጅቶች
ለባለሙያዎች ባዘጋጁት የጋዜጠኝነትና ኮሙኒኬሽን፣ የጤና ጋዜጠኝነት እና የምርመራ ጋዜጠኝነት ስልጠናዎች ላይ በዋና አሰልጣኝነት አገልግሏል።የምስራች የጋዜጠኝነት
ስልጠና ማዕከል ለሚሰጣቸው ስልጠናዎችም የኮሙኒኬሽን፣ የወንጀልና የትራፊክ አደጋ ዘገባዎች መምህር ሆኖ ሰርቷል።
መላኩ ከመደበኛ
ስራው በተጨማሪ ጦማር ፣ ሮዝ ፣ ዘ ፕሬስ እና ዕለታዊ አዲስ ለተሰኙ የያኔው ጋዜጦችና መጽሄቶች ፍሪላንስ ዘጋቢ ሆኖም
ሰርቷል። በተለይም በማህበራዊ ጉዳዮች ላይ ፣ በወንጀል እና
በምርመራ ዘገባዎቹ በርካታ አንባቢዎችን ሊያፈራ ችሏል። በቀድሞ ጊዜ የሸዋጌጥ ተካልኝ፣ መላከ ብርሃን ተስፋይ በመጨረሻም
እስከቅርብ ጊዜ “ኮከብ አሳየ” የመላኩ የብዕር ስሞች ሆነው ዘልቀዋል።
አዲስ ጉዳይ-ትልቁ የነጻነት ቤት
መላኩ ዋናውንና
በህይወቴ ትልቅ ቦታ የምሰጠውን ጋዜጠኝነት ጀመርኩ የሚለው ‹‹አዲስ ጉዳይ መጽሄትን በማኔጂንግ ኤዲተርነት ከተቀላቀለ በኋላ
በሰራቸው ስራዎች ነው። ‹‹አዲስ ጉዳይ መጽሄት ከ2004 ጀምሮ በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ በሙሉ ቀለም እና በየሳምንቱ
በመዘጋጀት ቀዳሚ የሆነ በብዙሃን ዘንድ እጅግ የሚከበርና እና የሚሰደድ ፣ መንግስት ተጽዕኖ ፈጣሪ ብሎ ከፈራቸውና በመጨረሻም
ሆን ብሎ ካፈረሳቸው መጽሄቶች ግንባር ቀደሙ ነበር።
የግል ፕሬሱ ዋና ሰው እንዳልካቸው ተስፋዬ
መላኩ “የማይታየው
የወቅቱ የግል ፕሬስ ዋና ሰው” ይለዋል እንዳልካቸውን፡፡ እንዳልካቸው በኢትዮጵያ የህትመት ስራ ውስጥ በጋዜጣ እና በመጽሄት
የማከፋል ስራ ውስጥ ጉልህ ድርሻ ያበረከተ ነው፡፡ እንዳልካቸው አዲስ ጉዳይ መጽሄትን ማሳተም ሲጀምር መላኩ በምስረታው ላይ
ትልቁን ድርሻ አበርክቷል፡፡ ።አዲስ ጉዳይ ከሮዝ መጽሄት በኋላ ተሻሽሎና በጥናት ተቀርጾ ለለውጥ እና ለማህብረሰብ እውቀት
የተፈጠረ ፣ እንደዘመን አቻው ‹‹አዲስ ነገር›› ጋዜጣ በብዙ ባለሙያዎች የተደራጀ ባለራዕይ መጽሄት ሆኖ እንዲቀጥል ከፍ ያለ
ሙያዊ አስተዋጽኦውን በፍቅር አበርክቷል::
ስለአዲስ ጉዳይ
ባልደረቦች ሳነሳ ክሪኤቲቭ ዲዛይነሮቹ ዘሪሁን አሰፋ እና
መስፍን አድነው መጠቀስ አለባቸው፡፡ እነዚህ
ባለሙያዎች መጽሄቷ በሌይ አውት ምርጥ እንድትሆን ትልቅ ስራ የሰሩ ናቸው፡፡
እነበእውቀቱ ስዩም፣ ዳንኤል ክብረት፣ ረ/ፕ አበባው አያሌው፣ ሰለሞን
ተሰማ ጂ. ፣ ቀሲስ ኤፍሬም፣ ዶክተር ብርሃኔ ረዳኢ፣ ሰርጸ ፍሬ ስብሃት፣ ዶክተር ዳኛቸው አሰፋ ፣ሃብታሙ ስዩም ወዘተ
የሚጽፉበት የወቅቱ የምሁራንና የአዋቂዎች ድምጽ የሚሰማበት መጽሄት አዲስ ጉዳይ እንደነበር ያስታውሳል።
መላኩ እንዳልካቸው
ተስፋዬን “የምንጊዜም የኔ ምርጥ ሰው ነው” የሚለው ይህንን ሁሉ ምሁርና አዋቂ ሰው በየዘርፉ አሰባስቦ ለሃገሪቱ በታሪክ
የማይዘነጋ ምርጥ የህትመት ውጤት መፍጠር የቻለ ሰው በመሆኑ ነው ይላል። ለ4 አመታት ከ100 በላይ እትሞችን
በማቅረብየዘለቀችው አዲስ ጉዳይ ደረጃዋን ጠብቃ መጓዟን ባለሙያዎች ይመሰክራሉ፡፡ ነፍስ ሄር ኢብራሂም ሻፊ ፣ ዮሃንስ ካሳሁን፣
አስማማው ሃይለጊዮርጊስ፣ ቴዎድሮስ ተክለአረጋይ፣ እንዳለ ተሺ የሙያ ባልደረቦቹ ሲሆኑ ከቴዎድሮስ ተክለአረጋይ ውጪ አዳዲሶቹን
የስታፍ አባላት እነአዚዛ መሃመድ እና መድሃኒት ረዳን ጨምሮ ሁሉም በመንግስት ማስፈራሪያ እና ክስ ሳቢያ ዛሬ በውጭ ሃገራት
በተለያየ ስራና ህይወት ላይ የሚገኙ ባለሙያዎች ናቸው። መላኩ ጋዜጠኛ ኢብራሂም ሻፊ ዛሬን በህይወት ቆሞ አለማየቱ ይቆጨኛል
ይላል። ኢብራሂም ሻፊ በሁሉ ልብ ውስጥ የእግር እሳት የሆነ፣ ስደት ላይ ሳለ ህይወቱ ያለፈ ምርጥ ማንም የማይስተካከለው አዋቂ
የስፖርት ጋዜጠኛ ነው ይላል መላኩ።
“እንዳልካቸው
ተስፋዬ ለዚህች ሃገር የፕሬስ ነጻነት ማበብ እና አንባቢ የሚገባውን ክብር እንዲያገኝ ሙሉ ነገሩን አጥቶም ቢሆን ከአደጋ ጋር
ተጋፍጦ የታተረ ሊሸለም የሚገባው ታላቅ ሰው ሰው ነው” ይላል
መላኩ የአዲስ ጉዳይ ባልደረቦቹንና ጓደኞቹን ሲያስታውስ።
መላኩና አዲስ ጉዳይ መጽሄት
መላኩ ይህንን
መጽሄትነት መንግስት እስኪዘጋው ድረስ በማኔጂንግ ኤዲተርነት መርቷል። የታፈኑ እውነቶች፣ ፍቅርና ወንጀል፣ ቢዝነስቴይመንት፣
ትዳር እና ፍቅር፣ ማንን እንማ የመሳሰሉትን በጊዜው ከፍ ያለ አንባቢ የነበራቸውን አምዶችን በባለቤትነት ይዞ ሰርቷል። በተለይ
“ዐቢይ ጉዳይ” በተሰኘ አምድ ላይ ይቀርቡ ከነበሩ በርካታ የፖለቲካ ትንታኔዎች ውስጥ የርሱ ስራዎችም ብዙ ናቸው። በታፈኑ ዕውነቶች አምድ ስር የሚቀርቡ በማህበራዊ ችግሮች ላይ ያተኮሩና
በተግባር ለውጥ ያመጡ ዘገባዎችን እንዲሁም የወንጀል አምድ ስር
የሚቀርቡ እውነተኛ ታሪኮችን እያዘጋጀ መጽሄቱ በመንግስት እስከተዘጋበት 2007 ዓ.ም መጨረሻ ድረስ አዲስ ጉዳይ ላይ
አገልግሏል።
መላኩ በዚህ መጽሄት
በጊዜው የነበረውን የፖለቲካ ስርዓት ችግሮች ገንቢ በሆነ መንገድ በማሳየት የህዝብ መብት እንዲከበር እና መንግስትም ተገቢ
የአስተዳደር ተግባሩን በብቃት እንዲወጣ የመልካም አስተዳደር እና የፖለቲካ ባህል ለውጥ እንዲመጣ የበኩሉን ሙያዊ ድርሻ
ተወጥቷል።ለዚህም ነው “በጋዜጠኝነት ህይወቴ ለአላማ የሰራሁበትና የሙያ መስዋዕትነት የከፈልኩበት ዘመን ያ ጊዜ ነው” ብሎ
የሚኮራው።
መላኩ-ወደ አርትስ ቲቪ
በዘመኑ በፕሬስ ላይ
በነበረው ጫና እና ምቹ ያልሆነ ከባቢ ለሶስት አመታት ያህል ጋዜጠኝነትን በመደበኛነት ከመስራት ርቆ በኮርፖሬት ኮሙኒኬሽን ስራ
ላይ የቆየው መላኩ ከለውጡ ጋር ተያይዞ አዲስ ጮራ በፈነጠቀው የሃገሪቱ ፕሬስ ላይ ዳግም ለመስራት ከመስከረም 2019 ጀምሮ
አሁን ድረስ በአፍሪካ ሬይነሰንስ ቴሌቪዠን ሰርቪስ (አርትስ ቴሌቪዠንን) በዜና ክፍል ሃላፊነት በመቀላቀል እስከ ቺፍ ኦፕሬሽን
ኦፊሰርነት በደረሰ የሃላፊነት ቦታ አገልግሏል። በብዙሃን ዘንድ እውቅና ያገኘበትን “ዐቢይ ጉዳይ” በመባል በሚታወቀውን
የውይይት ፕሮግራም በመቅረጽና በአዘጋጅነትና አቅራቢነት በመስራት የሃገራችንን የፖለቲካ እና ማህበራዊ ዲስኮርስ ባህሎች
ወደውይይት እና መግባባት ባህል ለማምጣት የበኩሉን ሙያዊ ሃላፊነት እየተወጣም ይገኛል።
“ፍቅርና ወንጀል” የመላኩ መጽሀፍ
መላኩ በጋዜጠኝነት
የስራ ዘመኑ ከመደበኛነት ከሰራባቸው ከላይ የተጠቀሱ ሚዲያዎች ባሻገር
ከ1994 ዓ.ም ጀምሮ በወንጀል እና በማህበራዊ ጉዳዮች አምደኝነት እንደ ጦማር፣ ዕለታዊ አዲስ እና ዘ-ፕሬስ እንዲሁም ጽጌረዳ እና ሮዝ የመሳሰሉ በዘመኑ ተነባቢ ጋዜጦችና
መጽሄቶች ላይ ሰርቷል። በተለይም ኮከብ አሳየ በሚል የብዕር ስም “ፍቅርና ወንጀል” እንዲሁም “የታፈኑ ዕውነቶች” በተሰኙ
አምዶች ላይ ያቀርባቸው በነበሩ በወንጀል እና ማህበራዊ ችግሮች ላይ ያተኮሩ የምርመራ ዘገባዎች ብዙ አንባቢያን ያውቁታል።
እነዚህን ታሪኮች በማሰባሰብ በ2009 ዓ.ም “ፍቅርና ወንጀል” የተሰኘ አንድ መጽሃፍም ለንባብ አብቅቷል። የበርካታ መጽሃፍትም
አርታኢ ነው። በቅርቡም ግዮን በተባለ መጽሄት ላይ በፍሪላንስ ለብዙ ዕትሞች የዘለቀ የከቨር ስቶሪዎች ጸሃፊ ሆኖም ሰርቷል።
ስልጠና
መላኩ ብርሃኑ በስራ
ዘመኑ ከጋዜጠኝነት ሙያው ጋር ለተያያዙ ዓለም አቀፍ ኮንፈረንሶች፣ ስልጠናዎችና ጥናታዊ ጉብኝቶች 11 ወደሚጠጉ
የአፍሪካ፣የአውሮፓ፣የእስያ እንዲሁም የመካከለኛውና የሩቅ ምስራቅ ሃገራት ተጉዟል። ይህ ጋዜጠኛ በአብዛኛው በጤና ዘገባ ፣
በተጨማሪም በህገ-ወጥ ስደት እና በሌሎች ርዕሶች ላይ በተዘጋጁ የሚዲያ ዘገባ ውድድሮች ተሳታፊ በመሆን ለንባብ ባበቃቸው ስራዎቹ
ከ International Centre For Journalists የአለምአቀፍ ሽልማት ተሸላሚ ነው። በተጨማሪም የ Africa
Media Initiative የአንድ አህጉራዊ ሽልማት 2nd place AMI award አሸናፊ ሲሆን በሃገር ውስጥ ውድድሮችም የ
IOM, PANOS, EAJA , ICFP ENHIA እና MoH ሃገር
አቀፍ የጋዜጠኝነትናሚዲያ ዘገባዎች ሽልማቶች እና ግራንቶች
አሸናፊ ባለሙያ ነው።
የሙያ
ማህበራት
በሙያ ማህበራት
ተሳትፎ በኩልም መላኩ ቀዳሚው የኢትዮጵያ ፕሬስ ካውንስል ሲመሰረት በአካባቢ ጋዜጠኞች ማህበር ተወካይነት ፈራሚ ሲሆን የቀድሞው
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ጋዜጠኞች ህብረት ፣የኢትዮጵያ አካባቢ
ጋዜጠኞች ማህበርም የቦርድ ሰክረታሪ ሆኖ አገልግሏል። በቀድሞው የኢትዮጵያ ጤና ጋዜጠኞች ኢኒሺየቲቭ እና የአፍሪካ የጤና
ጋዜጠኞች ማህበርም በአባልነትና በተጨማሪም በኢትዮጵያ የቤተሰብ ጤና ጋዜጠኞች ማህበር ውስጥ በልዩ አባልነትም አገልግሏል።
በአሁኑ ወቅት በኢትዮጰያ አርታኢያን ማህበር የስራ አስፈጻሚ አባል እንዲሁም በኢትዮጲያ ሚዲያ ሴክተር አሊያንስ ውስጥ አባል
ነው።
ሌሎች…..
በኮሚዩኒኬሽን ዘርፍ
ኖቬ ኮንሰልቲንግ በተባለ የጣሊያን ኩባንያ ውስጥ ቺፍ ኮሙኒኬሽን ስፔሻሊስትነት፣ በጊፍት ቢዝነስ ግሩፕ በኮርፖሬት ኮሙኒኬሽን
እና ፕሮሞሽን ስራ አስኪያጅነት ሰርቷል። በአሁኑ ወቅትም በቡና ኢንተርናሽናል ባንክ የኮሙኒኬሽን እና ፕሮሞሽን ስራ አስኪያጅ
ነው።
መላኩ ከ24 አመት
በዘለቀ የጋዜጠኝነት ህይወቱ ለአንዲትም ቀን ቢሆን አቅሙን ሳይቆጥብ ሰርቷል፡፡ አብረውት ይሰሩ የነበሩ በግልጽ እንደተናገሩት
መላኩ ለሌሎች አርአያ የሚሆን ሁለ-ገብ እውቀትን የተላበሰ ባለሙያ ነው፡፡ ይህን ክህሎቱንም ጽሁፎቹን በጥልቀት ከማንበብ
መረዳት ይቻላል፡፡ መላኩ በቅድመ-ዝግጅት ያምናል፡፡ ስለ አንድ ጉዳይ ከመስራቱ በፊት በበቂ ሁኔታ ይዘጋጃል፡፡ ይህን
በማድረጉም ስራዎቹ ብስለትን የተላበሱ ሊሆኑ ችለዋል፡፡
ቤተሰባዊ ህይወት
መላኩ ከወይዘሮ
ሊዲያ ተስፋዬ ጋር ትዳር በመመስረት ሰንፔር መላኩ፣ ሚካኤል መላኩ እና አሜን መላኩ የተባሉ 3 ልጆችን አፍርቷል። “ቀሪው
ዘመን በኮሙኒኬሽን ለውጥ የማመጣበት፣ በጋዜጠኝነቴም ሃገሬን የምጠቅምበት፣ በመምህርነት ትውልድ የምቀርጽበት ዘመን ነው” ይላል
መላኩ።
መላኩ ብርሃኑን
በየዕለቱ ጽሁፎቹንና ምልከታዎቹን በሚያጋራበትና በርካታ ተከታዮች ባሉት የፌስቡክ አድራሻው
አስተያየቶች
አስተያየት ይለጥፉ