
178.ጣሰው ተፈራ ዘለቀ የለጌው ባለሟል ጣሰው ተፈራ ፣ መምህርና ጋዜጠኛ ነው፡፡ በአሁኑ ሰአት መኖሪያውን በአሜሪካ ያደረገ ሲሆን ለ20 አመታት በለገዳዲ ሬድዮ በቅዳሜና እሁድ የመዝናኛ ፕሮግራሞች ላይ ያገለገለ ባለሙያ ነው፡፡ ብዙዎች ገና በተማሪነት ዘመናቸው የለገዳዲ ደጃፍ የረገጡ ሲሆን በትህትና እነዚህን ወጣቶች ካሳተፉ ባለውለታዎች አንዱ ጣሰው ተፈራ ነው፡፡ የመዝገበ-አእምሮ የሚድያ ሰዎች ታሪክ አዘጋጅ እዝራ እጅጉ ገና በታዳጊነቱ የመጀመሪያውን ተሰጥኦ እንዲያወጣ በር የከፈተለት ጣሰው ተፈራ ነው፡፡ ታዲያ ይህ ለብዙዎች ስኬታማ መሆን ምክንያት የሆነ ሰው ማነው? የሚለውን እንደሚከተለው እናቀርባለን፡፡ ትውልድ እና እድገት ጣሰው ተፈራ የተወለደው በአሩሲ ከሁሩታ ከተማ 12 ኪ.ሜ ያህል ርቃ በምትገኘው ሎዴ ጫንጌ በምትባል ቦታ ነው ።ጊዜውም ጥቅምት 27 ፤1950 ዓ.ም ነበር ። የሬዲዮ ፕሮግራም አዘጋጁ ጣሰው የአርሶ አደር ልጅ ሲሆን፣ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቱን በአርብ ገበያ በአሁኑ ሎዴ ጫንጌ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተከታትሏል ። የአንደኛ ደረጃ ተማሪ እያለ የመምህር ብርሃኑን እና የመምህር አሰፋን ውለታ የሚረሳ አይደለም ።ፊደል እንዲለይ ከማድረግ ጀምሮ እስከ ወስጄው ላስተማረው ድረስ ከፍተኛ ፍቅር ነበራቸው፡፡ ስድስተኛ ክፍል ሲደርስ የምንጊዜም የማይረሳው የህብረተሰብ ትምህርት መምህሩን መምህር ተክለብርሃን ነው።መምህሩ በሚያምር ድምጹ ከጠረጴዛው ላይ በመቀመጥ ስለሜሶፖታሚያ ታሪክ የሚያነብላቸውን ዛሬው ድረስ አይረሳውም ። መምህር...